እስራኤል ደቡባዊ ሊባኖስ ወስጥ በፈጸመችው ጥቃት 13 ሰዎች ተገደሉ
እስራኤል ደቡባዊ ሊባኖስ ወስጥ በፈጸመቻቸው የአየር ጥቃቶች አራት ሴቶች እና አንድ ሕጻን ልጅን ጨምሮ 13 ሰዎች መገደላቸውን የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የእስራኤል ጦር ጥቃት በፈጸመበት ናባቴህ አውራጃ በተፈጸመው ድብደባ ከተገደሉት ስምንት ሰዎች ውስጥ ሁለት ሴቶች እና አንድ ሕጻን እንደሚገኙበት ተገልጿል።
ሁለት ሴቶችን ጨምሮ አራት ሰዎች የተገደሉት ደግሞ ሲዶን አውራጃ ውስጥ ሲሆን አንድ ሰው አኢን ባል በተባለው ስፍራ አንድ ሰው ተገድሏል። በአጠቃላይ 32 ሰዎች ተጎድተዋል።
የሊባኖስ ተኩስ አቁም ለሦስት ሳምንታት ቢራዘምም በእስራኤል እና ሄዝቦላህ መካከል የሚደረገው ውጊያ ቀጥሏል። ሄዝቦላህ ዛሬ ቅዳሜ ሊባኖስ ውስጥ የሚገኙ የእስራኤል ወታደሮች እና ወታደራዊ ተሽከርካሪዎችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።
የእስራኤል ጦር አንድ ሐሙስ ዕለት ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተደረገ ውጊያ አንድ ወታደሩ መገደሉን ገልጿል። ከመጋቢት ወዲህ የተገደሉ የእስራኤል ወታደሮች ብዛት 17 ደርሷል።
የመጀመሪያው የ10 ቀናት ተኩስ አቁም ይፋ የሆነው የእስራኤል እና ሊባኖስ አምባሳደሮች ዋሽንግተን ውስጥ ካደረጉት ንግግር በኋላ ነበር።
ምንም አይነት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የሌላቸው ሁለቱ አገራት ከአውሮፓውያኑ 1993 ወዲህ በከፍተኛ ባለሥልጣናት ደረጃ ንግግር ሲያደርጉ የዋሽንግተኑ የመጀመሪያው ነው።
ሁለቱ አገራት ለሁለተኛ ጊዜ ከተገናኙ በኋላ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ዕለት ተኩስ አቁሙ ለሦስት ሳምንት መራዘሙን አስታውቀዋል። ትራምፕ፤ “ራሷን ከሄዝቦላህ እንድትጠብቅ” ከሊባኖስ ጋር እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ውስጥ ባይሳተፍም እስራኤል ስምምነቱን የምታከብር ከሆነ ቡድኑም ለተኩስ አቁሙ እንደሚገዛ ጠቁሞ ነበር።