የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የኢራን ጦርነት ባለበት በመቆሙ የኮንግረስን ፈቃድ መጠየቂያ ጊዜ አላለፈም አሉ
የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት የትራምፕ አስተዳደር የኢራን ጦርነትን ባለበት በማቆሙ ከኮንግረስ ፈቃድ ለማግኘት የሚያስፈልገው የ60 ቀናት ገደብ አልተጠናቀቀም ሲሉ ተከራከሩ።
ሄግሴት ይህንን ያሉት ሐሙስ ዕለት በሴኔት አባላት የቀረበላቸውን ጥያቄ ሲመልሱ ነው። ትራምፕ በይፋ ኮንግረስን ኢራን ላይ ስለሚፈጽሙት ጥቃት ካሳወቁ 60 ቀን የሚሞላው ዛሬ አርብ ነው።
ኮንግረስ ጦርነት እንዲቀጥል በ60 ቀናት ውስጥ ይሁንታ የማይሰጥ ከሆነ ፕሬዝዳንቱ “የዩናይትድ ስቴትስ ጦርን መጠቀም እንደሚያቋርጡ” በአሜሪካ ሕግ ተደንግጓል።
አንድ ከፍተኛ የአስተዳደሩ ባለሥልጣን ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት የተጀመረው በሚያዚያ ወር ስለሆነ “ተቋርጧል” ሲሉ ተናግረው ነበር።
አሜሪካ እና ኢራን የተኩስ አቁም ከመስማማት በዘለለ የተጀመረው ውይይት ውጤት ሊያስገኝ አልቻለም።
ቴህራን ለድርድር የሚሆን አዲስ ነጥቦችን በፓኪስታን በኩል መላኳን የኢራኑ የዜና ወኪል ኢርና ዘግቧል። የዜና ወኪሉ ዝርዝር ጉዳዮችን አልተዘገበም። የፓኪስታን ባለሥልጣናት እቅዱ ለአሜሪካ መሰጠቱን የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ተናግረዋል።
ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ከዘጋች በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨምሮ የነበረ ቢሆንም የኢራን አዲስ የሰላም እቅድ ከተሰማ በኋላ ቅናሽ አሳይቷል።
ወሽመጡ ሙሉ በሙሉ ተዘግቶ ለሁለት ወራት ያህል በመቆየቱ ተጽዕኖው የዓለም ምጣኔ ሃብት ላይ እየታየ ነው።
ሐሙስ ዕለት ሴናተሮች ላቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት መከላከያ ሚኒስትሩ “አሁን ያለነው በተኩስ አቁም ውስጥ ነው፤ ይህም በእኛ መረዳት የ60 ቀኑ ሰዓት ለጊዜው ቆሟል ወይም በተኩስ አቁሙ ቆሟል የሚል ነው” ብለዋል።