ትራምፕ ውድቅ ያደረጉት የኢራን እቅድ ከኒውክሌር ንግግር በፊት ሆርሙዝ እንዲከፈት የሚጠይቅ መሆኑ ተዘገበ
ኢራን በፓኪስታን በኩል ያቀረበችው እና ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያልተደሰቱበት አዲሱ የሰላም እቅድ ስለ ኒውክሌር ፕሮግራም የሚደረግ ንግግር በይደር ተይዞ የሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት እና አሜሪካ የጣለችው የባሕር ጉዞ እገዳ እንዲያበቃ የሚጠይቅ መሆኑን ሮይተርስ ዘገበ።
የዜና ወኪሉ ስማቸው ያልተጠቀሰ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣንን ጠቅሶ፤ ቴህራን የኒውክሌር ድርድሩን ለሌላ ጊዜ ለማቆየት ያቀረበችው እቅድ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚረዳ ትልቅ እርምጃ ነው ብላ ታምናለች ሲል ዘግቧል።
በአዲሱ እቅድ መሠረት ጦርነቱ የሚቋጨው እስራኤል እና አሜሪካ በድጋሚ ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይከፍቱ ዋስትና ሰጥተው እንደሚሆን ዘገባው ጠቅሷል። ኢራን በምላሹ ዘግታው የከረመችውን ወሳኙን የሆርሙዝ ወሽመጥ የምትከፍት ሲሆን አሜሪካም ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የጣለችውን እገዳ ታነሳለች።
በመጀመሪያው ደረጃ ንግግር ይህ ከተከናወነ በኋላ በኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ላይ ስለሚጣል ገደብ እና ማዕቀቦችን ስለማንሳት ድርድር ይደረጋል። ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለማገድ ብትስማማ እንኳ አሜሪካ ለቴህራን ለሰላማዊ ዓላማ ዩራኒየም የማበልጸግ መብት እውቅና እንድትሰጥ እንደምትጠየቅ የሮይተርስ ዘገባ ያመለክታል።
ሮይተርስ ያነጋገራቸው ባለሥልጣን፤ "በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ለስምምነቱ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር እንዲቻል ይበልጥ ውስብስብ በሆነው የኒውክሌር ጉዳይ ላይ የሚደረገው ድርድር ወደ መጨረሻው ደረጃ እንዲዛወር ተደርጓል" ብለዋል።
ኢራን ከዚህ ቀደም ያቀረበችው እና ፕሬዝዳንት ትራምፕ ውድቅ ያደረጉት ሌላ እቅድም በተመሳሳይ የኒውክሌር ጉዳይ በቅድሚያ ንግግር የሚደረግበት ጉዳይ እንዳይሆን የሚጠይቅ ነበር።
ቴህራን አዲስ እቅድ ማቅረቧን ካስታወቀች በኋላ አስተያየት የሰጡት ፕሬዝዳንት ትራምፕ እንዳላስደሰታቸው በመናገር “ልስማማበት የማልችለውን ነገር እየጠየቁ ነው” ብለዋል።
“ስምምነት ላይ መድረስ ይፈልጋሉ። እኔ አልረካሁበትም፤ ስለዚህ የሚፈጠረውን እናያለን” ሲሉም ተናግረዋል።
ፕሬዝዳንቱ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖራት የሚያደርግ ስምምነት ላይ ሳይደረስ ጦርነቱ ሊቋጭ እንደማይችል በተደጋጋሚ ተናግረዋል። ኢራን በበኩሏ የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላም የሚውል መሆኑን በአጽንኦት ገልጻለች።