አሜሪካ በኢራን ኃይሎች እና የሚሳዔል ይዞታዎች ላይ እርምጃ ልትወስድ መሆኑ ተነገረ
በባሕረ ሰላጤው አካባቢ የተሰማሩት የአሜሪካ ኃይሎች በኢራን ሠራዊት እና ይዞታዎች ላይ እርምጃ እንዲወስዱ መመሪያ እንደተላለፈላቸው ተዘገበ።
የአሜሪካ የዜና ድረ ገጽ የሆነው አክሲዮስ አንድ የአገሪቱን ከፍተኛ ባለሥልጣን ጠቅሶ እንደዘገበው በቀጣናው ያሉ የአሜሪካ ኃይሎች በሚወስዱት እርምጃ ዙሪያ የነበረው መመሪያ ተለውጧል።
ስማቸው ያልተጠቀሰው ባለሥልጣን ተናገሩት እንደተባለው በባሕረ ሰላጤው የተሰማሩት የአሜሪካ ኃይሎች “የኢራንን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ፈጣን ጀልባዎች ወይም የሚሳዔል ማስወንጨፊያ ቦታዎችን” ዒላማ እንዲያደርጉ ፈቃድ ተሰጥቷቸዋል።
የአሜሪካ ሠራዊት ይህንን እርምጃ እንዲወስድ የታዘዘው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል በሚያልፉ መርከቦች ላይ ተጨባጭ ስጋት ይፈጽማሉ ብለው ባመኗቸው ዒላማዎች ላይ ነው።
የአሜሪካ ሠራዊት እርምጃ የሚወስድባቸው ዒላማዎችን በተመለከተ አዲስ መመሪያ የወጣው አሜሪካ በሆርሙዝ በኩል ለሚተላለፉ መርከቦችን ከለላ እንደምትሰጥ ካሳወቀች በኋላ ነው።
በዚህም ሳቢያ በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ያለው ውጥረት እየተባባሰ ሲሆን፣ ኢራን በአሜሪካ የጦር መርከቦች ላይ የሚሳዔል ጥቃት መፈጸሟን ስታስታውቅ አሜሪካ ደግሞ ዜናውን በማስተባበል መርከቦቿ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልጻለች።