ትራምፕ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ የቆሙ መርከቦችን “እየመራች” ልታስወጣ መሆኑን ተናገሩ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
እሁድ ዕለት ትራምፕ መርከቦቻቸው በሆርሙዝ ወሽመጥ የቆሙባቸውን አገራት እንደሚያግዙ ተናገሩ።
“ለኢራን፣ ለመካከለኛው ምሥራቅ እና ለዩናይትድ ስቴትስ ደህንነት ሲባል ለአገራት መርከቦቻቸውን እየመራን እገዳ ከተጣለበት የውሃው አካል እንደምናስወጣላቸው ነግረናቸዋል። ስለዚህ በነጻነት ወደሚቀጥለው ጉዳይቸው መሄድ ይችላሉ” ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።
ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ ቆመው ያሉት እና አሜሪካ ድጋፍ ልታደርግላቸው መሆኑን የነገረቻቸው የየትኞቹ አገራት መርከቦች እንደሆኑ አላሰወቁም።
ትራምፕ “ፕሮጀክት ፍሪደም” (የነጻነት ፕሮጀክት) ሲሉ የጠሩት ይህ መርከቦችን ከወሽመጡ የማስወጣት ሂደት ሰኞ ዕለት እንደሚጀመር ተናግረዋል።
ትራምፕ ይህ መርከቦቸን የማስወጣት ሂደትን ለማደናቀፍ የሚሞክር ካለ “የኃይል እርምጃ” እንደሚወስዱ አስጠንቀቅቀዋል።
ኢራን ከየካቲት ወር መጨረሻ ጀምሮ በወሽመጡ ላይ የሚደረግ እንቅስቃሴን ሙሉ በሙሉ አግዳለች።
ዩናይትድ ስቴትስ እንዲሁ ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እና እንዳይወጡ እገዳ ጥላለች።
የኢራን አብዮታዊ ዘብ አዛዥ የነበሩት እና አሁን የፓርላማ አባል የሆኑት ኢብራሂም አዚዝ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ማንኛውም የአሜሪካ ጣልቃ ገብነት” እንደ “የተኩስ አቁም ጥሰት” ይቆጠራል ብለዋል።
ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ልጥፋቸው ላይ የአሜሪካ ተወካዮች ከኢራን ጋር “በጣም አዎንታዊ” የሆነ ውይይት ማካሄዳቸውን ጠቅሰው “ሁላችንንም በጣም በጎ ወደ ሆነ ነገር ይመራል” ብለዋል።
አክለውም መርከቦችን ከወሽመጡ የማስወጣት ዘመቻ “የሰብዓዊነት እርምጃ” መሆኑን ተናግረው በአሜሪካ፣ ኢራን እና ሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ስም የሚደረግ መሆኑን ተናግረዋል።
ትራምፕ በዚህ ልጥፋቸው ላይ ከቴህራን ጋር ያለው ትብብር በምንም መልኩ እንደሚስተናገድ ያሉት ነገር የለም።
ትራምፕ ". . . የመርከብ እንቅስቃሴው ምንም ጥፋት ያልፈጸሙ ሰዎችን፣ ኩባንያዎችን እና አገራትን ለማስለቀቅ የሚደረግ ብቻ ነው" ሲሉ አብራርተዋል።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በፕሮጀክት ፍሪደም ላይ 15,000 ወታደሮች፣ ዒላማቸውን ለይተው የሚመቱ ሚሳዔል ማምከኛዎች እንዲሁም ከ100 በላይ አውሮፕላኖች እንደሚሳተፉ አስታውቋል።
በባሕረ ሰላጤው ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ወደ 20,000 የሚገመቱ ባህረተኞች መንቀሳቀሻ አትተው መቆማቸው ይገመታል።
ለመርከቦቹ እና ሠራተኞቻቸው በየጊዜው እየቀነሰ የመጣው አቅርቦት እና የባሕረተኞቹ አካላዊ እና የአእምሮ ጤና አሳሳቢነት እያደገ መጥቷል።
የዓለም 20 በመቶ የሚሆነው ነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፈው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ነው።

