ቀጥታ, ኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ አሜሪካ ምላሽ መስጠቷን ገለጸች

ኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ ከአሜሪካ ምላሽ ማግኘቷን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ። የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አሜሪካ የሰጠችው ምላሽ በፓኪስታን በኩል እንደደረሳቸው እና እየተመለከቱት መሆኑን መናገራቸውን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል። አሜሪካ እስካሁን ድረስ ለቴህራን የሰላም ዕቅድ ምላሽ መሰጠቷን በይፋ አላሳወቀችም። ይሁን እንጂ ፕሬዚዳንት ትራምፕ እሁድ ዐዕለት ለእስራኤሉ ካን ኒውስ ዕቅዱ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ተናግረዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

ኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ አሜሪካ ምላሽ መስጠቷን ገለጸች

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ የቆሙ መርከቦችን “እየመራች” ልታስወጣ መሆኑን ተናገሩ

    ከአሜሪካ የጦር መርከብ ላይ ጄት እየተንደረደረ ሲነሳ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እሁድ ዕለት ትራምፕ መርከቦቻቸው በሆርሙዝ ወሽመጥ የቆሙባቸውን አገራት እንደሚያግዙ ተናገሩ።

    “ለኢራን፣ ለመካከለኛው ምሥራቅ እና ለዩናይትድ ስቴትስ ደህንነት ሲባል ለአገራት መርከቦቻቸውን እየመራን እገዳ ከተጣለበት የውሃው አካል እንደምናስወጣላቸው ነግረናቸዋል። ስለዚህ በነጻነት ወደሚቀጥለው ጉዳይቸው መሄድ ይችላሉ” ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ ቆመው ያሉት እና አሜሪካ ድጋፍ ልታደርግላቸው መሆኑን የነገረቻቸው የየትኞቹ አገራት መርከቦች እንደሆኑ አላሰወቁም።

    ትራምፕ “ፕሮጀክት ፍሪደም” (የነጻነት ፕሮጀክት) ሲሉ የጠሩት ይህ መርከቦችን ከወሽመጡ የማስወጣት ሂደት ሰኞ ዕለት እንደሚጀመር ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህ መርከቦቸን የማስወጣት ሂደትን ለማደናቀፍ የሚሞክር ካለ “የኃይል እርምጃ” እንደሚወስዱ አስጠንቀቅቀዋል።

    ኢራን ከየካቲት ወር መጨረሻ ጀምሮ በወሽመጡ ላይ የሚደረግ እንቅስቃሴን ሙሉ በሙሉ አግዳለች።

    ዩናይትድ ስቴትስ እንዲሁ ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እና እንዳይወጡ እገዳ ጥላለች።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ አዛዥ የነበሩት እና አሁን የፓርላማ አባል የሆኑት ኢብራሂም አዚዝ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ማንኛውም የአሜሪካ ጣልቃ ገብነት” እንደ “የተኩስ አቁም ጥሰት” ይቆጠራል ብለዋል።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ልጥፋቸው ላይ የአሜሪካ ተወካዮች ከኢራን ጋር “በጣም አዎንታዊ” የሆነ ውይይት ማካሄዳቸውን ጠቅሰው “ሁላችንንም በጣም በጎ ወደ ሆነ ነገር ይመራል” ብለዋል።

    አክለውም መርከቦችን ከወሽመጡ የማስወጣት ዘመቻ “የሰብዓዊነት እርምጃ” መሆኑን ተናግረው በአሜሪካ፣ ኢራን እና ሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ስም የሚደረግ መሆኑን ተናግረዋል።

    ትራምፕ በዚህ ልጥፋቸው ላይ ከቴህራን ጋር ያለው ትብብር በምንም መልኩ እንደሚስተናገድ ያሉት ነገር የለም።

    ትራምፕ ". . . የመርከብ እንቅስቃሴው ምንም ጥፋት ያልፈጸሙ ሰዎችን፣ ኩባንያዎችን እና አገራትን ለማስለቀቅ የሚደረግ ብቻ ነው" ሲሉ አብራርተዋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በፕሮጀክት ፍሪደም ላይ 15,000 ወታደሮች፣ ዒላማቸውን ለይተው የሚመቱ ሚሳዔል ማምከኛዎች እንዲሁም ከ100 በላይ አውሮፕላኖች እንደሚሳተፉ አስታውቋል።

    በባሕረ ሰላጤው ጦርነት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ወደ 20,000 የሚገመቱ ባህረተኞች መንቀሳቀሻ አትተው መቆማቸው ይገመታል።

    ለመርከቦቹ እና ሠራተኞቻቸው በየጊዜው እየቀነሰ የመጣው አቅርቦት እና የባሕረተኞቹ አካላዊ እና የአእምሮ ጤና አሳሳቢነት እያደገ መጥቷል።

    የዓለም 20 በመቶ የሚሆነው ነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፈው በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ነው።

  2. ኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ አሜሪካ ምላሽ መስጠቷን ገለጸች

    የኢራን መሪዎች ምስል የታተመበት ባንዲራ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ ከአሜሪካ ምላሽ ማግኘቷን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አሜሪካ የሰጠችው ምላሽ በፓኪስታን በኩል እንደደረሳቸው እና እየተመለከቱት መሆኑን መናገራቸውን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    አሜሪካ እስካሁን ድረስ ለቴህራን የሰላም ዕቅድ ምላሽ መስጠቷን በይፋአላሳወቀችም። ይሁን እንጂ ፕሬዚዳንት ትራምፕ እሁድ ዕለት ለእስራኤሉ ካን ኒውስ ዕቅዱ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ተናግረዋል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን የቴህራን ባለ 14 ነጥብ የሰላም ዕቅድ ዋሺንግተን ጦሯን ከድንበር አካባቢ እንድታርቅ፣ የኢራን ወደቦች ላይ ያለቸውን እገዳ እንድታነሳ እንዲሁም የትኛውም ግጭት፣ እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምትፈጽመውን ጨምሮ እንዲቆም የሚጠይቅ ነው ሲሉ ዘግበዋል።

    ዕቅዱ በሁለቱ አገራት መካከል በሰላሳ ቀናት ውስጥ ስምምነት እንዲደረስይጠይቃል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን አክለውም የሰላም ዕቅዱ ሁለቱም ተፋላሚ ወገኖች አሁን ያለውን የተኩስ አቁም ከማራዘም ይልቅ “ጦርነቱን በማስቆም” ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ ይጠይቃል።

    መገናኛ ብዙኃኑ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይን ጠቅሰው “አሁን ባለው ደረጃ ስለ ኒውክሌር ድርድር የለም” ማለታቸውን ዘግበዋል።

    ኢራን በተደጋጋሚ የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላማ ብቻ የሚውል መሆኑን ትናገራለች።

    ነገርግን ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ባይኖራትም ዩራኒየምን የጦር መሣሪያ ለማምረት በሚያስችል ደረጃ ያበለጸገች ብቸኛ አገር ናት።