ቀጥታ, የአሜሪካ እና የኢራን ጥቃት ሲቀጥል የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ

አሜሪካ ለተከታታይ ቀናት በኢራን ላይ እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት ተከትሎ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት እና ሆርሙዝ ወሽመጥ የኢራን የአጸፋ ጥቃት ዒላማ ሲሆኑ የነዳጅ ዋጋም ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ። ባለፉት ሳምንትታት በርካታ መርከቦች በተወንጫፊዎች በመመታታቸው የነዳጅ ጫኝ መርከቦች እንቅስቃሴ በከፍተኛ መጠን ቀንሷል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ዱባይ በጦርነቱ የሸሹ ጎብኚዎችን ለመሳብ ቅናሽ እና ማበረታቻ ልትሰጥ ነው

    ባደ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በጦርነቱ ምክንያት የዱባይ ቱሪስት መዳረሻዎች ባዶ ሆነዋል

    የተበባሩት አረብ ኤምሬትስ ታዋቂዋ የቱሪስት ከተማ ዱባይ በጦርነት ምክንያት የተዳከመውን የቱሪስት ፍሰት ለማነቃቃት ለወራት የሚቆይ ልዩ ቅናሽ በመስጠት ጎብኚዎችን ልታበረታታ መሆኗን አስታወቀች።

    ቤተሰቦቻቸውን እና ጓደኞቻቸውን ወደ ዱባይ ለጉብኝት የሚጋብዙ የከተመዋ ነዋሪዎች ከ800 ዶላር በላይ ቅናሽ እና ልዩ መስተንግዶ እንደሚቀርብላቸው የዱባይ የመገናኛ ብዙኃን ጽህፈት ቤት ዛሬ ረቡዕ አስታውቋል።

    ይህ አስከ መጪው ዓመት ጥቅምት ድረስ የሚቆየው ማበረታቻ የተዘጋጀው በባሕረ ሰላጤው እየተካሄደ ያለው ጦርነት በግዛቲቱ የቱሪዝም ዘርፍ ላይ ያስከተለውን ጫና እና ጉዳት ለመቀነስ ነው።

    የዱባይ አስተዳደር በድረገጹ ላይ እንዳመለከተው ከአሁን ጀምሮ አስከ ጥቅምት ወር መጨረሻ ድረስ ቤተሰቦቻቸውን እና ጓደኞቻቸውን ለጉብኝት የሚጋብዙ ነዋሪዎች የሚያርፉበት ሆቴል፣ የምግብ እና የጉብኝት ቦታዎች ትኬቶችን ጨምሮ የተለያዩ ጥቅማጥቆሞችን ያገኛሉ።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ዋነኛዋ የቱሪስት መዳረሻ የሆነችው አንዷ በየዓመቱ 19.5 ሚሊዮን ጎብኚዎችን ስታስተናግድ ቆይታለች።

    ነገር ግን አሜሪካ እና አስራኤል በኢራን ላይ ባካሄዱት ከአንድ ወር በላይ በዘለቀ ጦርነት የቱሪስት ፍሰቷ በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል።

    በጦርነቱ ወቅት ኢራን የተባበሩት አረብ ኤምሬትስን ዒላማ ያደረገች ሲሆን፣ ሆቴሎች እና ታላላቅ ተቋማቷ ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።

    በዚህም የተነሳ በወሳኙ የጎብኚዎች ጊዜ በተቀሰቀሰው ጦርነት ምክንያት በርካታ ቱሪስቶች አገሪቱን ለቅቀው መውጣታቸው ተዘግቧል።

    ሚያዝያ ላይ የተኩስ አቁም ከተደረገ በኋላ የተወሰኑ ጎብኚዎች ወደ አገሪቱ ቢገቡም የቀደመው የቱሪስቶች ፍሰት አልተመለሰም። በዚህም የተነሳ የዱባይ መንግሥት በጦነርቱ ጫና የደረሰባቸውን የንግድ ተቋማትን ለማገዝ የ400 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አቅርቧል።

  2. የየመን ሁቲዎች ዛሬም በቀይ ባሕር ላይ መርከቦች እንዳይተላለፉ አገዱ

    የጭነት መርከብ በቀይ ባሕር ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በቀይ ባሕር ግዙፍ መርከቦች ነዳጅ እና ሌሎች ጭነቶችን ይዘው የሚተላለፉበት ወሳኝ መስመር ነው

    የየመን ሁቲዎች በሳዑዲ አረቢያ ላይ የባሕር እንቅስቃሴ ገደብ ከጣሉ በኋላ ተጨማሪ መርከቦች በቀይ ባሕር በኩል እንዳያልፉ መከልከላቸው ተዘገበ።

    ማክሰኞ ዕለት ከሳዑዲ ወደብ የተነሱ ሦስት ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው አቅጣጫቸውን የቀየሩ ሲሆን፣ ዛሬ ረቡዕ ደግሞ አራት የሳዑዲን ነዳጅ የጫኑ መርከቦች በደቡባዊ ቀይ ባሕር በኩል ማለፍ በመከልከላቸው ወደ ኋላ መመለሳቸው ተዘግቧል።

    ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ውስጥ የገባችው የኢራን አጋር የሆኑት እና የየመን የባሕር ዳርቻ የሚቆጣጠሩት ሁቲዎች ሰኞ ዕለት ወደ ሳዑዲ የሚሄዱ እና ከሳዑዲ የሚነሱ መርከቦች በቀይ ባሕር በኩል ወደ ባብ ኤል መንደብ ማለፍ እንደማይችሉ አስጠንቅቀዋል።

    ዛሬ አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ ከተገደዱት መርከቦች መካከል ሁለቱ ወደ ሰሜን በማቅናት በሱዩዝ ካናል በኩል ጉዟቸውን እንዳደረጉ ተዘግቧል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የአውሮፓ ባሕር ኃይል ከአሜሪካ፣ ከእስራኤል እና ከሳዑዲ አረቢያ ጋር ግንኙነት ያላቸው መርከቦች ለጊዜው በቀይ ባሕር በኩል ጉዞ እንዳያደርጉ አስጠንቅቋል።

    ለዚህም ምክንያቱ ከአገራቱ ጋር የሚያያዙ መርከቦች በሁቲ ታጣቂዎች ጥቃት ሊፈጸምባቸው የሚችልበት ከፍተኛ ዕድል ስላላቸው መሆኑን በመጥቀስ በጉዞ ላይ ያሉም ከሆነ አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ መክሯል።

    በቀይ ባሕር የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ የተፈጠረው ስጋት በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ ለወራት ካለው ቀውስ ጋር ተደማምሮ በዓለም የነዳጅ አቅርቦት ላይ ጫና ስለሚፈጥር የዋጋ ጭማሪ ማስከተሉ እንደማይቀር እየተነገረ ነው።

  3. የአሜሪካ እና የኢራን ጥቃት ሲቀጥል የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ

    እየፈጸመችው ያለው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ ለተከታታይ ቀናት በኢራን ላይ እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት ተከትሎ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት እና ሆርሙዝ ወሽመጥ የኢራን የአጸፋ ጥቃት ዒላማ ሲሆኑ የነዳጅ ዋጋም ከፍተኛ ጭማሪ አሳየ።

    በተለይ ዮርዳኖስ ባለፉት ተከታታይ ቀናት በኢራን ሚሳዔሎች ተከታታይ ጥቃቶች የተፈጸሙባት ሲሆን፣ ሚሳዔሎቹን ለማክሸፍ በምታደርገው ጥረት ተወጥራለች።

    የእስራኤል አጎራባች በሆነችው ዮርዳኖስ ላይ በዛሬው ዕለት ስድስት የኢራን ሚሳዔሎች እንደተተኮሱባት እና የአገሪቱ ጦር ሠራዊት አራቱን ማክሸፉን አስታውቋል። ሁለቱ ደግሞ ሰው በማይኖርባቸው ራቅ ያሉ ስፍራዎች ላይ መውደቃቸውን ፔትራ የተባለው የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የእስራኤል ኤይላት ከተማ ነዋሪዎች የቀረጹት እና በቀይ ባሕር ዳርቻ ላይ ከምትገኘው አቃባ ከተማ ላይ የሚነሳ ጭስ ወደ ሰማይ ሲወጣ የሚያሳዩ ቪዲዮዎች መታየታቸውን አሶሺየትድ ፕሬስ ዘግቧል።

    እስራኤል በዮርዳኖስ ላይ የተፈጸሙት ጥቃቶች የፈጠሩት ጭስ ከድንበሯ ባሻገር መታየታቸው ስጋት የፈጠረባቸው የእስራኤል ባለሥልጣናት የኢራን ጥቃት ወደ ግዛታቸው ሊሸጋገር እንደሚችል እያስጠነቀቁ ነው።

    ዮርዳኖስ የአሜሪካ ጦር ሠራዊት አባላት እና አውሮፕላኖች በግዛቷ ውስጥ እንዲሰፍሩ በመፍቀዷ በተደጋጋሚ የኢራን ጥቃት ዒላማ ሆናለች። በተጨማሪም ኩዌት እና ባህሬን ባለፉት ቀናት የኢራን ጥቃት ደርሶባቸዋል።

    በፋርስ ባሕረ ሰላጤው አካባቢ የሚደረገው የኢራን እና የአሜሪካ ጦርነት ዳግም ከተቀሰቀሰ በኋላ የሆርሙዝ ወሽመጥ ደኅንነት አደጋ ላይ በመውደቁ መርከቦች ስጋት ተደቅኖባቸዋል።

    ባለፉት ሳምንትታት በርካታ መርከቦች በተወንጫፊዎች በመመታታቸው የነዳጅ ጫኝ መርከቦች እንቅስቃሴ በከፍተኛ መጠን ቀንሷል።

    በዚህም ሳቢያ በጦርነቱ መቆም ከፍተኛ ቅናሽ አሳይቶ የነበረው የነዳጅ ዋጋ እያሻቀበ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ከሰኔ ወር መጀመሪያ ወዲህ ከፍተኛ የሆነው ደረጃ ላይ ደርሷል።

    በዛሬው የብሬንት የነዳጅ ገበያ ተመን መሠረት የአንድ በርሜል ዋጋ ወደ 94 ዶላር በመድረስ ከአንድ ወር በላይ በሆነ ጊዜ ውስጥ ዋጋው ከፍተኛ መጠን ላይ ደርሷል።

    ኢራን በአሜሪካ በሚፈጸምባት ጥቃት ምክንያት በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት እና በሆርሙዝ ወሽመጥ መመሪያዋን በሚጥሱ መርከቦች ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አጠናክራለች።

    በዚህም የተነሳ ለመርከቦች ያወጣችውን “መመሪያ አላከበሩም” ያላቻቸውን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሊያቋርጡ የነበሩ ሁለት መርከቦች ማስቆሟን እና ጥቃት መፈጸሟን አስታውቃለች።

  4. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መቆጣጠሯ “አደገኛ አካሄድ” መሆኑን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናገሩ

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ከኢራን ጋር የተፈጠረውን ቀውስ ለመግታት በሚል ዋሽንግተን ለድርድር “አሁንም ዝግጁ ብትሆንም” ቴህራን ግን “ድርድርን በቁም ነገር እንደማትወስድ” ገለጹ።

    ሩቢዮ ይህንን የተናገሩት ከደቡብ ምሥራቅ እስያ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ ሲሆን፤ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መቆጣጠሯ “አደገኛ አካሄድ ነው” ሲሉም ገልጸዋል።

    ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣን ሰኞ ዕለት ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንደተናገሩት፤ ቴህራን ለ10 ቀናት የተኩስ አቁም እንዲደረግ ከአሸማጋዮች ጥያቄ ቀርቦላታል።

    የኢራን የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ትናንት ማክሰኞ ወደ ፓኪስታን ተጉዘው ከአገሪቱ ወታደራዊ አዣዥ ጋር ተወያይተዋል።

    ሩቢዮ ከደቡብ ምሥራቅ እስያ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ባደረጉት ውይይት፤ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መቆጣጠሯ “አደገኛ አካሄድ” መሆኑን ጠቅሰው የዚህም ዳፋ ከመካከለኛው ምሥራቅ ይሻገራል ብለዋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የምትፈጽመው ጥቃት 11ኛ ቀኑን ይዟል።

    የአሜሪካ ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) እንዳለው በኢራን ላይ እየደረሰ ያለው ተከታታይ ጥቃት ዓላማው በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ “ለንግድ መርከቦች አስጊ የሆነ አቅሟን ለማዳከም” ነው።

    ሩቢዮ “ዓለም አቀፍ የውሃ መተላለፊያን አንድ አገር የሚቆጣጠር፣ ከመርከቦች ክፍያ የሚጠይቅ እና የማይከፍሉትን ዒላማ የሚያደርግበት አካሄድ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚኖር ከሆነ አደገኛ አካሄድ ይፈጠራል” ብለዋል።

    “አደገኛ” ያሉት አካሄድ ቀጣናውን ጨምሮ በሌሎች የዓለም ክፍሎችም “ሊደገም” እንደሚችልም አስጠንቅቀዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ደርሰው የነበረ ቢሆንም በሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደር ጉዳይ ዳግመኛ ወደ ውጊያ ተመልሰዋል።

    ኢራን አሜሪካ እየፈጸመችባት ላለው ጥቃት በምላሹ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ የጦር ሰፈሮቿን ዒላማ አድርጋ የአጸፋ እርምጃ እየወሰደች ነው።

    ኢራን በተደጋጋሚ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደር ላይ መብት እንደሌላት ገልጻለች።

    ቴህራን “ከ30 በላይ የንግድ መርከቦች ላይ ጥቃት ፈጽማለች” ሲል የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ከስሷል።

    ማርኮ ሩቢዮ ባደረጉት ንግግር “ጉዳዩ ቀላል ነው። ኢራን ሕጋዊ መነሻ ሳይኖራት የሆርሙዝ ወሽመጥን የመቆጣጠር መብትን እየጠየቀች ነው” ብለዋል።

  5. ጉንዳኖችን ጣፋጭ ምግብ ለመሥራት የተጠቀመው ሬስቶራንት ባለቤት በእስራት እንዲቀጣ ተጠየቀ

    ጉንዳኖች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የደቡብ ኮሪያ ዐቃቤ ሕግ ጉንዳኖችን ተጠቅሞ ጣፋጭ ምግብ ያቀረበው ሬስቶራንት ባለቤት በአንድ ዓመት እስራት እንዲቀጣ ጠየቀ።

    በአገሪቱ ሕግ ለምግብነት እንዲውሉ ፈቃድ ከተሰጣቸው 10 ነፍሳት መካከል ጉንዳኖች አልተካተቱም።

    ፌንጣ እና አንበጣ ለምግብነት እንዲውሉ ፈቃድ ከተሰጣቸው ነፍሳት ውስጥ ይገኙበታል።

    ዐቃቤ ሕግ ሬስቶራንቱ 20 ሚሊዮን የኮሪያ ዎን (13,510 ዶላር) እንዲቀጣም ጠይቋል።

    ሚኬሊን በተባለው የፈረንሳይ ተቋም የሚሰጠው የቅንጡ ሬስቶራንቶች ደረጃ ያለው ምግብ ቤቱ ባለቤት ጉንዳኖችን መጠቀሙን ቢያምንም “በውስን መጠን ብቻ” ጥቅም ላይ ውለዋል ብሏል።

    በረዶ ከፍራፍሬ ጋር ተዋህዶ በአይስ ክሬም መልክ የሚሠራበት ‘ሶርብትስ’ በተባለው ጣፋጭ ምግብ አናት ላይ በስሱ ብቻ ጉንዳኖች መነስነሳቸውን ገልጿል።

    ተመጋቢዎች ጉንዳን ያልተነሰነሰበትን ጣፋጭ ምግብ ማዘዝ እንደሚችሉም ተናግሯል።

  6. ስድስት የአንድ ቤተሰብ አባላት የሆኑ ፍልስጤማውያን በእስራኤል ጥቃት መገደላቸው ተገለጸ

    ቤተሰቦቻቸው የተገደሉባቸው ፍልስጤማውያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ስድስት የአንድ ቤተሰብ አባላትን ጨምሮ ቢያንስ 12 ፍልስጤማውያን በእስራኤል ጥቃት መገደላቸውን የሕክምና ባለሙያዎች አስታወቁ።

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ፣ ምዕራባዊ አል-ሳባራ መንደር በፈጸመችው ሦስት ተከታታይ ጥቃቶች ፍልስጤማውያኑ መገደላቸውን ገልጸዋል። ጥቃቶቹን የሚያሳዩ ተንቀሳቃሽ ምሥሎችም ወጥተዋል።

    ከተገደሉት ፍልስጤማውያን አንዱ የሆነው የፊራስ አል-ማስሪ ወንድም ለቢቢሲ እንደገለጸው፤ ፊራስ እና ባለቤቱ ሳላሳቤል እንዲሆም ሦስት ሴት ልጆቻቸው እና አንድ ወንድ ልጃቸው በእሳት ተቃጥለው ሞተዋል።

    ልጆቻቸው ፋርያል፣ ሳልማ፣ አሚራ እና ናይም ይባሉ ነበር።

    የእስራኤል ጦር በበኩሉ ዒላማ ያደረገው የሐማስ ይዞታን እንደሆነ ገልጿል። የጥቃቱ ያደረሰውን ጉዳትንም እያጤነ እንደሆነ አስታውቋል።

    ማክሰኞ ከሰዓት በሌላ በማዕከላዊ ጋዛ አል-ሳማር መንደር በደረሰ የእስራኤል የአየር ተጨማሪ አራት ሰዎች መሞታቸውን የሕክምና ባለሙያዎችን በመጥቀስ የፍልስጤም መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር ይሄንን ጥቃት በተመለከተ አስተያየት አልሰጠም።

    እስራኤል እና ሐማስ የተኩስ አቁም ከተፈራረሙ በኋላ ቢያንስ 1,168 ፍልስጤማውያን መገደላቸውን የጋዛ የጤና ሚኒስቴር ገልጿል።

  7. አሜሪካ ለሳዑዲ አረቢያ የሲቪል ኒውክሌር ተቋም ልትገነባ መሆኑ ተዘገበ

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና አልጋ ወራሽ ልዑል ቢን ሰልማን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና አልጋ ወራሽ ልዑል ቢን ሰልማን

    አሜሪካ እና ሳዑዲ አረቢያ የሲቪል የኒውክሌር መርሃ ግብር ለመገንባት የሚያስችል ሥራ ለመጀመር ስምምነት ሊፈርሙ እንደሆነ ኒው ዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ዘገበ።

    ስምምነቱ ዛሬ ረቡዕ እንደሚፈረም እየተነገረ ሲሆን፣ ይህም በመካከለኛው ምሥራቅ ዋነኛ የነዳጅ ዘይት አምራች ለሆነችው ሳዑዲ አዲስ እርምጃ ነው ተብሏል።

    በኢራን ጦርነት የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የነዳጅ አቅርቦቷ የቀነሰው ሳዑዲ አረቢያ ስምምነቱን እንደምትፈርም የተገለጸው የየመን ሁቲ ታጣቂዎች በቀይ ባሕር በኩል በሚያልፉ መርከቦቿ እንቅስቃሴ ላይ ዕገዳ ከጣሉ በኋላ ነው።

    ኒው ዮርክ ታይምስ ሁለት ስማቸው ያልተገለጸ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ጠቅሶ የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ዛሬ ረቡዕ ስምምነቱን በይፋ ለመፈረም ዕቅድ እንዳለው ዘግቧል።

    ይህ ስምምነት ለአሜሪካ የኒውክሌር ኢንዱስትሪ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ገንዘብ እንደሚያስገኝ የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ገልጿል።

    ዎል ስትሪት ጆርናል እደዘገበው ደግሞ አሜሪካ ከሳዑዲ ጋር የምትፈርመው የ30 ዓመታት ስምምነት ሁለቱ አገራት በሚያደርጉት ጥቃት አስፈላጊነቱ ከተረጋገጠ የአሜሪካ ኩባንያዎች ለሳዑዲ የዩራኒየም ማበልጸጊያ ተቋም ይገነባሉ።

    ነገር ግን አንዳንድ የአሜሪካ ምክር ቤት አባላት እና የእስራኤል ባለሥልጣናት የሳዑዲ የሲቪል ኒውክሌር ግንባታ የጦር መሳሪያ ለመሥራት ሊውል ይችላል በሚል ተቃውሟቸውን እያሰሙ ነው።

  8. አሜሪካ በኢራን ጦርነት 37.5 ቢሊዮን ዶላር ማውጣቷን የመከላከያ ሚኒስትሩ ተናገሩ

    ፒት ሄግዜት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ በኢራን ጦርነት ወደ 37.5 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ማውጣቷን የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግዜት ተናገሩ።

    ያለፈው ግንቦት ወር ላይ ከቀረበው የ8 ቢሊዮን ዶላር ወጪ የአሁኑ ከፍተኛ ነው።

    ሄግዜት ለአሜሪካ ሴኔት በሰጡት ማብራሪያ ለፔንታገን ተጨማሪ 87 ቢሊዮን ዶላር እንዲመደብ ጠይቀዋል። ከዚህ ገንዘብ 67 ቢሊዮን ዶላሩ በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚካሄድ ኦፕሬሽን የሚውል ነው ብለዋል።

    ሄግዜት ማብራሪያ በሚሰጡበት ወቅት ጦርነቱን የሚቃወሙ ሰዎች ድምጻቸውን በተደጋጋሚ በማሰማት ንግግራቸውን አቋርጠዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ በድጋሚ ወደ ግጭት ከተመለሱ ወዲህ ሄግዜት በካፒቶል ሂል ተገኝተው ማብራሪያ ሲሰጡ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    ሦስት አሜሪካውያን ወታደሮች በኢራን ጥቃት ተገድለዋል።

    ዋይት ሀውስ ለቀጣዩ በጀት ዓመት 1.5 ትሪሊዮን ዶላር እንዲፈቀድለት ጠይቋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የምታደርሰው ጥቃት 11ኛ ቀኑን ይዟል።

  9. ትራምፕ የኢራን የኒውክሌር ተቋም ላይ ጥቃት ለማድረስ ዛቱ

    በኢራን ላይ የደረሰው ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ በኢራን ላይ የምታደርሰው ጥቃት 11ኛ ቀኑን ይዟል። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከመሬት በታች የተገነባው የቴህራን የኒውክሌር ተቋም ላይ ጥቃት እንደሚሰነዝሩ ዝተዋል።

    ትራምፕ በኢራን፣ ናታንዝ የሚገኘውን ከምድር በታች የተገነባ የኒውክሌር ተቋም እንደሚመቱ መዛታቸውን ተከትሎ ቴህራን የአጸፋ ምላሽ እንደምትሰጥ አስጠንቅቃለች።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) እንዳለው በኢራን ላይ እየደረሰ ያለው ተከታታይ ጥቃት ዓላማው በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ “ለንግድ መርከቦች አስጊ የሆን አቅሟን ለማካደም” ነው።

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገበው በቴህራን የአየር መቃወሚያዎች ሥራ እንዲጀምሩ ተደርጓል።

    በታባሪዝ፣ ቻባሀር፣ ኮናርክ እና ቡሸህር ፍንዳታዎች መሰማታቸው ተዘግቧል። ቡሸህር የኢራን ብቸኛው የኒውክሌር ማብላያ ተቋም የሚገኝነት ነው።

    ኢራን አሜሪካ ላደረሰችባት ጥቃት በምላሹ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ የጦር ሰፈሮቿ ላይ ድብደባ አድርሳለች።

    ኢራን እና አሜሪካ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ደርሰው የነበረ ቢሆንም በሆርሙዝ ወሽመጥ አስተዳደር ጉዳይ ዳግመኛ ወደ ውጊያ ተመልሰዋል።

    ኢራን “ከ30 በላይ የንግድ መርከቦች ላይ ጥቃት አድርሳለች” ሲል የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ከስሷል።

    የኢራን ወታደራዊ ተቋማት፣ የባሕር ኃይል፣ የአየር ኃይል እና ሌሎችም የአገሪቱ የጦር መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት መፈጸሙንም አስታውቋል።

  10. “ኢራን እንድንወያይ አጥብቃ እየለመነች ነው”- ትራምፕ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን “ጦርነቱ እንዲቆም እንድንወያይ አጥብቃ እየለመነች ነው፤ ካልሆነ ግን ይወድማሉ” ሲሉ ዛቱ።

    ከሊባኖስ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን ጋር ሆነው በዋይት ሐውስ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ናቸው” ያሉት ኢራናውያን “ከእኛ ጋር መወያየት ይፈልጋሉ” ብለዋል።

    “ሆኖም ግን ትርጉም ያለው ውይይት የማይፈልጉ ከሆነ እኛ [መገናኘቱን] አንፈልግም” ሲሉም አክለዋል።

    የየመን ሁቲ አማጺያን በሳዑዲ አረቢያ የባሕር እንቅስቃሴ ላይ የጣሉትን ክልከላ በተመለከተ “ሁቲዎች የሳዑዲን ወደብ ከዘጉ አሜሪካ ጉዳዩን ትፈታዋለች” ብለዋል።

    ሁቲዎች ሳዑዲ አረቢያ ላይ የባሕር እንቅስቃሴ እገዳ መጣላቸውን አሳውቀዋል።

    ከሳዑዲ አረቢያ ነዳጅ ጭነው በቀይ ባሕር በኩል ሲቀዝፉ የነበሩ ሁለት ግዙፍ መርከቦች ከየመን ታጣቂ ቡድን ሁቲ በተሰጣቸው ማስጠንቀቂያ ምክንያት አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ መደረጋቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የሊባኖስ ፕሬዝዳንት በዋይት ሐውስ ትራምፕን አሞካሽተው “ጉብኝቱን ለረዥም ጊዜ ሲጠብቁት እንደቆዩ” ተናግረዋል።

    የእስራኤል እና ሊባኖስ ጦርነት እስከ ወዲያኛው ያከትማል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ጠቅሰው ይህም የትራምፕ “ሌጋሲ” ይሆናል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል።

    ትራምፕ ለሊባኖስ ብዙ ድጋፍ እንደሚያደርጉ እና አገሪቱ በሚገባት መጠን እንደሚያግዙ ተናግረዋል።

  11. የየመን ሁቲዎች ከሳዑዲ የተነሱ 2 ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በቀይ ባሕር እንዳያልፉ አገዱ

    ነዳጅ ጫኝ መርከብ (ፎቶ ከፋይል)

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ነዳጅ ጫኝ መርከብ (ፎቶ ከፋይል)

    ከሳዑዲ አረቢያ ነዳጅ ጭነው በቀይ ባሕር በኩል ሲቀዝፉ የነበሩ ሁለት ግዙፍ መርከቦች ከየመን ታጣቂ ቡድን ሁቲ በተሰጣቸው ማስጠንቀቂያ ምክንያት አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ መደረጋቸው ተዘገበ።

    የሳዑዲን የነዳጅ ምርት ጭነው ወደ ቻይና እና ሕንድ ሲጓዙ የነበሩት ሁለቱ መርከቦች ወደ መጡበት የተመለሱት ሁቲዎች በሳዑዲ አረቢያ ላይ የባሕር እንቅስቃሴ ዕቀባ መጣላቸውን ካሳወቁ በኋላ ነው።

    ከሳዑዲ ጋር በጠላትንት የሚተያዩት የኢራን የቅርብ ወዳጅ የሆኑት ሁቲዎች ማንኛውም ወደ ሳዑዲ የሚያቀኑ እና ከሳዑዲ ወደቦች የሚነሱ መርከቦችን ዒላማ እንደሚያደርጉ አሳውቀዋል።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው ከሳዑዲ የተነሱት ሁለቱ መርከቦች ከሁቲ ታጣቂዎች ማስጠንቀቂያ በኋላ ወደ ደቡባዊ የቀይ ባሕር መስመር መጓዛቸውን በመተው ፊታቸውን በማዞር ወደ ሱዩዝ ካናል አቅንተዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን በሚያደርጉት ጦርነት በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ኢራን በፈጠረችው ስጋት የተናጋው ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዘይት አቅርቦት የዋጋ ጭማሪ ያስከተለ ሲሆን፣ አሁን በቀይ ባሕር ላይ የተፈጠረው ስጋት የበለጠ ቀውሱን ያባብሰዋል ተብሎ ተሰቷል።

    በሁቲዎች ወደመጡበት እንዲመለሱ ከተደረጉት መርከቦች መካከል ዢ ሎነግ ያንግ የተባለው እጅግ ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ሁለት ሚሊዮን በርሜን ነዳጅ ጭና ሰኞ ዕለት ከሳዑዲ የቀይ ባሕር ዳርቻ ያንቡ ወደብ በመነሳት ወደ ቻይና እያቀና ነበረ።

    ሁቲዎች በቀይ ባሕር በኩል ከዚህ ቀደም ከአሜሪካ እና ከእስራኤል ጋር ግንኙነት አላቸው ያሏቸን መርከቦችን በማጥቃት የሚታወቁ ሲሆን፣ የተወሰኑ መርከቦችም መስመጣቸው አይዘነጋም።

  12. ኳታር በኢራን ለተፈጸመባት ጥቃት ካሳ እንዲከፈላት ጥያቄ አቀረበች

    የኳታር ሰንደቅ ዓላማ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኳታር ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በጻፈችው ደብዳቤ ኢራን በግዛቷ ላይ ለፈጸመችው ጥቃት ሙሉ ተጠያቂ መሆኗን ገልጻ ለደረሰባት ውድመት የካሳ ጥያቄ አቀረበች።

    ኳታር በደብዳቤዋ ላይ ከሁለት ሳምንት በፊት በሆርሙዝ ወሽመጥ አቅራቢያ የነዳጅ ጫኝ መርከቧን ዒላማ ማድረጓን እንዲሁም ከዚያ በኋላ በሁለት የተለያዩ ቀናት ደግሞ በግዛቷ ላይ የሚሳዔል ጥቃት መፈጸሟን ገልጻለች።

    የኳታር ባለሥልጣናት ኢራን በአገራቸው ላይ ከሳምንት በፊት የፈጸመችውን የሚሳዔል ጥቃት ተከትሎ ለማክሸፍ በተደረገው ጥረት መካከል ፍንጣሪዎች በመኖሪያ ስፍራ በመውደቃቸው አንድ ሕጻንን ጨምሮ ሦስት ሰዎች ተጎድተዋል ብለዋል።

    ደብዳቤው ጨምሮም ኢራን በኳታር ግዛት ላይ የፈጸመችው “የጠብ ጫሪነት ጥቃት” የአገሪቱን ሉዓላዊነት በግልጽ የጣሰ እና ለደኅንነቷ እንዲሁም ለግዛት አንድነቷ ቀጥተኛ ስጋት ነው በማለት አውግዞታል።

    ኳታር “ሉዓላዊነቷን፣ ደኅንነቷን እና የዜጎቿን ሕይወት ለመካከል ማንኛውንም ዓይነት አስፈላጊ እርምጃ ከመውሰድ ወደኋላ እንደማትል” አሳውቃለች።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚካሄደው ጦርነት መልሶ ካገረሸ በኋላ ኢራን የሚፈጸምባትን ጥቃት ለመበቀል በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ የአጸፋ ጥቃት እየፈጸመች ነው።

    ኢራንም በአካባቢው አገራት የምትጽማቸው ጥቃቶች ዒላማ ያደረጉት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን እና በአገራቱ ውስጥ የሰፈሩ ኃይሎቿን ነው ብላለች።

  13. የሊባኖስ ጦር እስራኤል ወደለቀቀችው መንደር እየገባ መሆኑን አስታወቀ

    ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በአሜሪካ አሸማጋይነት ባለፈው ወር በተደረሰው ስምምነት አማካኝነት የእስራኤል ኃይሎች ከያዟቸው የሊባኖስ ግዛቶች በመውጣታቸውን፤ የሊባኖስ ወታደሮች በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል ወደሚገኘው "የሙከራ (ፓይለት) ዞን" መግባት መጀመራቸው ተገለጸ።

    የሊባኖስ ጦር ባወጣው መግለጫ፣ ወታደራዊ አሃዶች በናባቲዬ አውራጃ በሚገኘው ዘውታር አል ጋርቢዬ መንደር መሰማራታቸውን አስታውቋል።

    የእስራኤል ጦር በበኩሉ ይህ የሙከራ ዞን እቅድ ተግባራዊ መሆን መጀመሩን ገልጿል።

    በዚህ እቅድ መሠረት እስራኤል ከሄዝቦላህ ጋር ግጭት በተደረገበት ወቅት ከተቆጣጠረቸው ግዛት ውስጥ ከተወሰነው ክፍል ወታደሮቿን ታስወጣለች። በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ደግሞ ትጥቅ እንዲፈታ ይጠበቃል።

    የወታደሮቹ ስምሪት የተሰማው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የሊባኖሱ መሪ ጆሴፍ አውን ዋሽንግተን ውስጥ ለሚያደርጉት ስብሰባ እየተዘጋጁ ባሉበት ወቅት ነው።

    የሊባኖሱ ፕሬዝዳንት፤ ትራምፕ እስራኤል ከቀረው የደቡብ ሊባኖስ ክፍል እንድትወጣ ጫና እንዲያደርጉ ይወተውታሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    የሊባኖስ ጦር ሄዝቦላህ የያዛቸውን አካባቢዎች ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ለሚያደርገው ጥረት እገዛ እንደሚጠይቁም ይታሰባል።

    ሊባኖስ፤ እስራኤል እና አሜሪካ ከኢራን ጋር ወደሚያደርጉት ጦርነት ተጎትታ የገባችው ሄዝቦላህ የኢራን ጠቅላይ መሪ ላይ የተፈጸመውን ግድያ ለመበቀል ወደ እስራኤል ሮኬቶችን ከተኮሰ በኋላ ነው።

    እስራኤል በመላው ሊባኖስን በመደብደብ እና በአገሪቱ ደቡባዊ ክፍል የሚገኝ ሰፊ ግዛትን በመውረር ምላሽ ሰጥታለች። መንደሮችንም አውድማለች።

    ሊባኖስ ውስጥ በተፈጸሙት የእስራኤል ጥቃቶች 800 ህጻናት፣ ሴቶች እና የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ 4,300 ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር አስታውቋል።

    የእስራኤል ባለሥልጣናት በበኩላቸው 37 የእስራኤል ወታደሮች እና አራት ንጹኃን መገደላቸውን ተናግረዋል።

  14. በአሜሪካ “የስደተኞች ፖሊስ ተቃዋሚ” የሆነ የቀድሞ ወታደር በጸጥታ መሥሪያ ቤት ደጅ እሳት አስነሳ

    በፌደራል ሕንፃ ፊት ለፊት የተነሳው እሳት

    የፎቶው ባለመብት, Robert Sullivan/AP

    በአሜሪካ ኒው ዮርክ ከተማ ውስጥ በሚገኝ የፌደራል ሕንፃ ፊት ለፊት እሳት ያስነሳ የቀድሞ ወታደር በቁጥጥር ሥር ዋለ።

    ግለሰቡ ሰኞ ዕለት እሳት ያስነሳው የፌደራል የምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ)፣ የስደተኞች እና ጉምሩክ ደንብ አስከባሪ (አይስ) እንዲሁ የአሜሪካ ዜግነት እና ኢሚግሬሽን አገልግሎት ተቋማት የሚገኙበት ’26 ፌደራል ፕላዛ’ የተሰኘው ሕንፃ ደጅ ላይ ነው።

    አንድሪው አራባካ የተባለው የ43 ዓመት ግለሰብ በአየር ግፊት የሚሰራ ፔሌት ሽጉጥ እንደተኮሰ እና ርችት እንደለኮሰ ተገልጿል።

    የፌደራል የጸጥታ አባላት ቆንጨራ እና ሌሎች መሣሪያዎችን ይዞ የነበረውን ይህን ተጠርጣሪ ይዘውታል።

    በዚህ ክስተት ማመልከቻው እየታየ የነበረ አንድ ስደተኛን ጨምሮ ሦስት ሰዎች ቀላል ጉዳት እንደደረሰባቸው ኤፍቢአይ ገልጿል።

    የአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት፤ ግለሰቡን “ፀረ አይስ አማጺ” ሲል ጠርቶታል። እሳቱን ከማያያዙ በፊት በሕንፃው መግቢያ ደረጃዎች ላይ ማቀጣጠያ በማፍሰስ እሳት ማስነሳቱንም ጠቅሷል።

    ቢቢሲ ስለ ጉዳዩ አስተያየት ለማግኘት ለአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት ጥያቄ አቅርቧል።

    የእሳት አደጋ ባለሙያዎች እሳቱን አጥፍተውታል።

    ኤፍቢአይ እንደሚገልጸው፤ ግለሰቡ "በክስተቱ ወቅት በርካታ መንግሥትን እና አይስን የሚቃወሙ ንግግሮችን” አሰምቷል።

    በኤፍቢአይ የኒው ዮርክ ምክትል ዳይሬክተር ጄምስ ባርናክል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ አራባካ ሁለት መጥረቢያ፣ አንድ ቆንጨራ፣ ሦስት ቢላ እና ርችት ይዞ እንደነበር ተናግረዋል።

    በያዘው የፔሌት ሽጉጥ ከአምስት እስከ ሰባት ጊዜ ወደ ሕንፃው አቅጣጫ እንደተኮሰም አስረድተዋል።

  15. ኢራን ባለፉት ቀናት የአሜሪካ ወታደሮችን መግደሏን እና የጦር ጄት ማውደሟን አስታወቀች

    የኢራን ሚሳዔሎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን አብዮታዊ እስላማዊ ዘብ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ተቋማት ላይ በፈጸመው ጥቃት የአሜሪካ ወታደሮችን መገደላቸውን እና የአገሪቱ የጦር አውሮፕላን መውደሙን አስታወቀ።

    አሜሪካ እየፈጸመችባት ላለው ተከታታይ ጥቃት ኢራን እየወሰደችው ባለው የአጸፋ እርምጃ ዮርዳኖስ፣ ኩዌት እና ባህሬን ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ይዞታዎችን ዒላማ አድርጋለች።

    ባለፉት ቀናት ከተፈጸሙት የኢራን ጥቃቶች መካከል ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኘው የአሜሪካ ሠራዊት ጦር ሰፈር ላይ በደረሰው ጉዳት “በርካታ” ወታደሮች መገደላቸውን የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

    ነገር ግን የኢራን አብዮታዊ ዘብ ላወጣው መግለጫ አሜሪካ አስካሁን ድረስ ምንም ዓይነት ምላሽ አልሰጠችም።

    ቀደም ሲል ግን ከአራት ቀናት በፊት ኢራን በፈጸመችው የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት ሦስት ወታደሮቹ እንደተገደሉበት የአሜሪካ ጦር አሳውቆ ነበር።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢራን በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ የአሜሪካ የራዳር እና የመከላከያ ተቋማት ላይ እየፈጸመችው ባለው ጥቃት በዮርዳኖስ መጠለያ ውስጥ ቆሞ የነበረ አንድ የአሜሪካ ኤፍ 15 የጦር አውሮፕላን መውደሙን አብዮታዊ ዘቡ ገልጿል።

    ኢራን ካለፈው ሳምንት ወዲህ በተለይ ዮርዳኖስ ውስጥ ተደጋጋሚ ጥቃቶች እየፈጸመች ሲሆን፣ የእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል እንዳስታወቀው በሚሳዔል እና ድሮን ጥቃቶቹ የሚሳዔል ጥቃት መከላከያ ሥርዓቶችም ዒላማ ሆነዋል።

    የአሜሪካው ጋዜጣ ኒው ዮርክ ታይምስ ወታደራዊ ባለሥልጣንን ዋቢ አድርጎ ሰኞ ዕለት እንደዘገበው፣ ኢራን ባለፈው ሳምንት ዮርዳኖስ በሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ውስጥ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች በርካታ ወታደሮች ቆስለዋል፤ ሄሊኮፕተሮችም ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር እንዳረጋገጠው በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ ኢራን በፈጸመችው ጥቃት ወደ 100 የሚጠጉ ወታደሮች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

  16. በአንድ ወር ወደ 100 የሚጠጉ የአሜሪካ ወታደሮች በኢራን ጥቃት መጎዳታቸውን የዋሽንግተን ባለሥልጣናት ተናገሩ

    የጦር አውሮፕላኖች

    የፎቶው ባለመብት, US Central Command

    ኢራን በዚህ ወር በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች ላይ በፈፀመቻቸው በርካታ የአየር ጥቃቶች 100 የሚጠጉ የአሜሪካ ሠራዊት አባላት ጉዳት እንደደረሰባቸው የአገሪቱ ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    የፔንታጎን ኃላፊ ቃል አቀባይ ሲን ፓርኔል የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ኒውስ በላኩት መግለጫ ቁጥሩን ያረጋገጡ ሲሆን ከሰኔ መጨረሻ ወዲህ 100 የሚሆኑ ሠራተኞቹ የተለያየ መጠን ጉዳት እንደደረሰባቸው ገልጸዋል።

    አብዛኛው ጉዳት ቀላል መሆኑን የገለጹት ቃል አቀባዩ፣ 96 በመቶ የሚሆኑት ወደ ሥራ ገበታቸው ተመልሰዋል ብለዋል።

    ባለፈው ሳምንት ብቻ በርካታ የአሜሪካ ወታደራዊ ሠራተኞች በዮርዳኖስ የጦር ሠፈር መጎዳታቸው ተዘግቧል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር ሁለት የአሜሪ ካወታደሮች በዮርዳኖስ በሚገኝ የጦር ሠፈር መገደላቸው እና ሌላ ወታደር የት እንደገባ አለመታወቁን ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ገልጿል።

    ሌላ ወታደር ደግሞ ኢራቅ ውስጥ ተገድሏል።

    በአሁን ወቅት በርካታ ወታደራዊ ሠራተኞች መጎዳታቸው የተሰማው፣ ትራምፕ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰው እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ያስችላል የተባለው የተኩስ አቁም ስምምነት "አብቅቷል" ካሉ በኋላ በአገራቱ መካከል እየተካሄደ ያለው ጦርነት ተባብሶ በቀጠለበት ጊዜ ነው።

    የአሜሪካ ጦር ከአንድ ሳምንት በላይ በተከታታይ በኢራን ዒላማዎች ላይ የምሽት ጥቃቶችን ፈፅሟል።

    ጥቃቱን የሚፈፅመው ኢራን በንግድ መርከቦች ላይ የምታደርሰውን ጥቃት ለማስቆም እንደሆነ ገልጿል።

    ኢራን በበኩሏ አሜሪካ ለምትፈፅምባት ጥቃት በዮርዳኖስ ፣ ኩዌት፣ ባሕሬን እና ሌሎች የአሜሪካ አጋር አገራት ላይ ጥቃት በመሰንዘር የአፀፋ ምላሽ እየሰጠች ነው።

  17. ኢራን ከአሜሪካ ጋር “ሙሉ ጦርነት” ውስጥ መገባቱን ስትገልጽ፤ ዋሽንግተን ለ10ኛ ተከታታይ ቀን ጥቃት ፈጸመች

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Iran's Presidential website/WANA/Reuters

    የአሜሪካ ጦር፣ የኢራንን በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚተላለፉ መርከቦች የማጥቃት አቅም "ይበልጥ ለማዳከም" ያለመ ነው ያለውን ጥቃት ለ10ኛ ተከታታይ ቀን ፈጽሟል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን በበኩላቸው፤ አገራቸው በአሁኑ ሰዓት ከአሜሪካ ጋር "ሙሉ ጦርነት" ውስጥ መሆኗን ተናግረዋል።

    “እውነታው ዛሬ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ሙሉ የሆነ ጦርነት ውስጥ መሆኗ ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቱ፣ “እውነታውን መገንዘብ እና የዚህን ተጋድሎ ተፈጥሯዊ መዘዞች መቀበል ይኖርብናል” ሲሉ ባወጡት መግለጫ አሳስበዋል።

    የሰኞ ሌሊቱ የዋሽንግተን ጥቃት የተፈጸመው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በፈጸመችው ጥቃት የአሜሪካ ወታደሮችን የገደለችው ኢራንን እንደሚቀጡ ከተገዘቱ በኋላ ነው።

    ባለፉት ቀናት በደረሱ ጥቃቶች ዮርዳኖስ ውስጥ ሁለት፣ በኢራቅ ደግሞ አንድ የአሜሪካ ወታደሮች ተገድለዋል።

    ኢራን ከትናንቱ ጥቃት በኋላ በወሰደቸው የአጸፋ እርምጃ፤ በሆርሙዝ ሲጓዙ የነበሩ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እንዲሁም ባህሬን እና ኩዌት ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ይዞታዎችን መምታቷን ‘ኢርና’ የተሰኘው የመንግሥት የዜና ወኪል ዘግቧል።

    በተመሳሳይ ሰዓት፣ ከዚህ ቀደም የተፈራረሙት የመግባቢያ ስምምነት የከሸፈባቸው አሜሪካ እና ኢራን በአሸማጋዮች አማካኝነት ዲፕሎማሲያዊ መልዕክት እየተለዋወጡ መሆኑን ቴህራን አስታውቃለች።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ በኤክስ ገጹ ባወጣው መግለጫ፤ በትናንቱ ጥቃት የኢራን "ወታደራዊ የዕዝ ማዕከላት፣ የባህር ኃይል አቅሞች፣ የሚሳዔል እና የድሮን ማስወንጨፊያ ስፍራዎች እንዲሁም የአየር መከላከያ ሥርዓቶች"መምታታቸውን ገልጿል።

    የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያደርጉትን ጉዞ እንደቀጠሉም በመግለጫው ጠቅሷል።

    ኢራን በበኩሉ ጥቃት በፈጸመችባቸው ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ውስጥ የነበሩ ባሕርተኞችን ለማውጣት የነፍስ አድን ቡድን መሰማራቱን አስታውቃለች። መርከቦቹ የተመቱት በወሽመጡ በኩል ለማለፍ በመሞከራቸው መሆኑን ኢርና ዘግቧል።

    የዮርዳኖስ መከላከያ ሠራዊት በበኩሉ ከኢራን የተወነጨፉ ሦስት ሚሳዔሎችን መትቶ መጣሉን ገልጿል። የኩዌት ጦርም ኢራን ድሮኖችን እንደጠለፈ አስታውቋል።

    ባሕሬን ደግሞ ከኢራን የተነሳ ድሮን የአየር መቆጣጠሪያ ስርዓቶቿን ዒላማ ቢያደርጉም በረራዎች አለመስተጓጎላቸውን ጠቅሳለች።

    የአሜሪካ ጦር በፈጸማቸው ጥቃቶች ታብሪዝ፣ ቻባሃር፣ ኮናራክ፣ ባንዳር ማህሻህር እና ባንዳር ኢማም ኾሜኒን ጨምሮ በርካታ ከተሞች መመታታቸውን ከፊል ይፋዊ የዜና ወኪል የሆነው ታስኒም ዘግቧል።

    በኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገባ መሠረት፣ ሆርሙዝ ወሽመጥን ለማቋረጥ የሞከሩ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ፍንዳታ ተከስቷል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ፤ መርከቦቹ "ደኅንነቱ ባልተጠበቀው እና በአደገኛው ደቡባዊ መስመር" እየተጓዙ ስለነበረ፤ “ፍንዳታ እንደተከሰተባቸው እና ጉዟቸው እንዲቋረጥ መደረጉን” አስታውቋል። የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በበኩሉ ይህንን ገለጻ አስተባብሏል።

  18. አንዲ በርንሃም የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ

    አንዲ በርንሃም

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    አንዲ በርንሃም በፈቃዳቸው ከሥልጣን የለቀቁትን የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ተክተው የአገሪቱ መሪ ሆኑ።

    የግሬተር ማንችስተር ከንቲባ የነበሩት በርንሃም፣ ዩናይትድ ኪንደግም ለመምራት በአምስት ዓመታት ውስጥ የተሾሙ ስድተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል። በአስር ዓመት ውስጥ ደግሞ ሰባተኛው የአገሪቱ መሪ ናቸው።

    አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በመጀመሪያ ንግግራቸው፤ “አገራችን ውስጥ የሚታየው የጎዳና አዳር እንዲያበቃ [አደርጋለሁ]” ብለዋል።

    ይህንን ለማስፈጸምም በአምስት ዓመታት ውስጥ ተጨማሪ 340 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚመደብ ተገልጿል።

    በዚህ ገንዘብ አማካኝነት 1,200 ቤቶች እንደሚገነቡ እንዲሁም በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ቢያንስ ለ3,000 ሰዎች “ከፍተኛ ድጋፍ” እንደሚደረግ ጽሕፈት ቤታቸው አስታውቋል።

    በርንሃም፤ መንግሥታቸው “ለሰዎች ውድቀት ከመክፈል ይልቅ፣ ስኬታቸው ላይ ኢንቨስት” እንዲያደርግ እንደሚፈልጉ በንግግራቸው ጠቅሰዋል።

    በተያዘው 2026 መጨረሻም አገሪቱ የምትመራበት አዲስ የ10 ዓመት ዕቅድ ይፋ እንደሚደረግ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ "የሕይወት መሠረታዊ ፍላጎቶችን በሕዝብ ቁጥጥር ስር ማድረግ" የሚያስችል ኢኮኖሚ እንደሚገነቡም ተናግረዋል።

    ከአውሮፓውያን 2016 ወዲህ የተሾሙ ሰባተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር መሆናቸውን በደንብ እንደሚገነዘቡ በመጥቀስም፤ “መለስ ብሎ መመልከቻ እና አዲስ ውሳኔ” ላይ መድረሻ ጊዜ እንዲኖር ጥሪ አቅርበዋል። ብሪታኒያ መረጋጋት ማግኘት እንዳለባትም በአጽንኦት አንስተዋል።

    ፖለቲከኞች “በበቂ ሁኔታ ጥሩ አልነበሩም” በማለት የተቹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የተሻለ ለመሆን ቃል ገብተዋል። ባለፉት 40 ዓመታት ውስጥ ያልታዩ ከፍተኛ ለውጦችን እንደያደርጉም ተናግረዋል።

  19. ሩሲያ በጭነት መርከብ ላይ በፈጸመችው ጥቃት 10 ሰዎች ተገደሉ

    ጥቃት የደረሰበት መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Andrii Sybiha

    ሩሲያ፣ ወደ ዩክሬኗ ከተማ ኦዴሳ ሲጓዝ በነበረ የጭነት መርከብ ላይ በፈጸመችው ጥቃት 10 ሰዎች ተገደሉ።

    ዩክሬን አየር ኃይል እንደገለጸው፣ በጊኒ ቢሳው ሰንደቅ ዓላማ የሚንቀሳቀሰው መርከብ በሩሲያ የክሩዝ ሚሳዔሎች የተመታው ትናንት እሁድ ነው። የደረሰው ጥቃት እሳት አስነስቷል።

    ከእሁድ ምሽት አንስቶ መርከቡ ላይ የነበሩ ሰዎችን ለመታደግ እና ለማግኘት የነፍስ አድን ሥራ እየተከናወነ ነው። የዩክሬን የባሕር ወደቦች ባለሥልጣን ሰኞ ጠዋት ይፋ ባደረገው መረጃ፤ ዘጠኝ ባሕረተኞች እንዲሁም ከካፒቴኖቹ አንዱ መገደላቸውን አስታውቋል።

    ባለፉት ሳምንታት ኦዴሳ ግዛት ተከታታይ ጥቃቶችን አስተናግዷል። ሩሲያ ሐምሌ ላይ ብቻ በግዛቱ ላይ በፈጸመቻቸው ጥቃቶች 28 ሰዎች መገደላቸውን የግዛቱ ዋና አስተዳዳሪ ኦሌህ ኪፐር ሰኞ ዕለት ለዩክሬን ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

    ሩሲያ በጥቁር ባሕር ላይ የሚጓዙ የጭነት መርከቦች ላይ የምትፈጽማቸው ጥቃቶችን ጨምረዋል።

    ከእነዚህ ጥቃቶች ውስጥ ብዙ ሰዎች የሞቱበት፣ እሁድ ዕለት በጊኒ ቢሳው ሰንደቅ ዓላማ የሚንቀሳቀሰው መርከብ ላይ የተፈጸመው ነው።

    ዓለም አቀፍ ባሕርተኞችን ይዘው በአብዛኛው በውጭ ሰንደቅ ዓላማ ሥር የሚንቀሳቀሱት እነዚህ የጭነት መርከቦች የሚጓዙት፣ ዩክሩን በቀራት ብቸኛ የኤክስፖርት ኮሪደር በኩል ነው። በሮማኒያ እና ቡልጋሪያ የባሕር ዳርቻዎች በኩል ከዩክሬን ወደ ቱርክ ያጓጉዛሉ።

    የሩሲያ ሙሉ ወረራ ከተጀመረ አንስቶ ላለፈው ከአራት ዓመት ተኩል በላይ የሚሆን ጊዜ በጥቁር ባሕር ላይ የሚደረገው ውጊያ በአብዛኛው አሸናፊ የነበረበት አይደለም።

    የሩሲያ ጦር አብዛኛውን የባሕር ዳርቻ በመቆጣጠሩ የዩክሬን መርከቦች በኦዴሳ ዙሪያ ወዳሉ አካባቢዎች ርቀው መጓዝ አይችሉም። ይሁን እንጂ ዩክሬን የምትፈጽማቸው የድሮን ጥቃቶች ሩሲያ ወታደራዊ አቅሟን በጥቁር ባሕር ምሥራቃዊ ክፍል ከሚገኙ የባሕር ኃይል ካምፖች እንዳታንቀሳቅስ አድርጓታል።

    ሩሲያ አሁን በዚህ ባሕር ላይ የምትፈጽመው ጥቃት ያጠናከረችው፤ የውጭ አገር ኩባንያዎች የዩክሬን ምርቶችን እንዳይገዙ እና የጥቁር ባሕር መተላለፊያን እንዳይጠቀሙ ለማድረግ እንደሆነ ይታመናል።

  20. ኢራን ከአሸማጋዮች የሰላም ዕቅድ እንደቀረበላት አስታወቀች

    የአሜሪካ ብንዲራ ከአጽም ጋር በተሳለበት ግድግዳ በኩል የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    አሜሪካ እና ኢራንን በድጋሚ ወደ ተኩስ አቁም ስምምነት ለመመለስ ያቀዱት አሸማጋዮች፣ አዲስ የሰላም ዕቅድ ማቅረባቸውን ቴህራን አስታወቀች።

    ሰኔ ላይ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነት ተፈራመው የነበሩት ሁለቱ አገራት፣ ላለፉት ሁለት ሳምንት ገደማ አንዳቸው በሌላቸው ላይ ከባድ ጥቃቶችን ሲፈጽሙ ቆይተዋል። የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ስምምነቱ አብቅቷል ብለዋል።

    ይህንን ስምምነት ዳግም ለመመለስ ያቀዱት አሸማጋይ አገራት የ10 ቀናት የተኩስ አቁም እንዲደረግ የሚጠይቅ የሰላም ዕቅድ ማቅረባቸውን ዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘግቧል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ዛሬ ሰኞ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ስለዚህ ጉዳይ ተጠይቀዋል። አሸማጋዮች ያዘጋጁትን ዕቅድ ለኢራን እንዳሳወቁ ቃል አቀባዩ አረጋግጠዋል።

    “በአሸማጋዮች ስለዘተጋጁት ዕቅዶች ገለጻ ተደርጎል፤ ዕቅዱም ደርሶናል። ነገር ግን ለአሁኑ ወደ ዝርዝር ጉዳዮች ባንገባ ይሻላል” ሲሉ ተጨማሪ መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል።

    ባለፉት ቀናት ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ መሆኑን የጠቆሙት ቃል አቀባዩ፤ “በአንዳንድ አሸማጋዮች የቀረቡ ዕቅዶች ለኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ መድረሳቸው የተረጋገጠ ነው” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደፊት ለመደራደር የሚጠይቁ ከሆነ የኢራን ምላሽ ምን እንደሚሆንም ጥያቄ የቀረበላቸው ቃል አቀባዩ ኢስማኤል ባጋይ፣ “ዲፕሎማሲ ወይም ጦርነት” የሚል አማራጭ ለኢራን “ጠቃሚ አይደለም” ሲሉ ተናግረዋል።

    “ራስን መከላከል ከዲፕሎማሲ ጋር አይጣጣምም ብሎ ማሰብ ትክክለኛ አመክንዮ አይደለም። [የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ] ሰይድ አባስ አራግቺ የሚያከናውኑት ሥራ እና [የመከላከያ ሚኒስትሩ] ሰይድ መጂድ የሚፈጽሙት ተግባር ተመሳሳይ ግብ የሚያሳኩ ናቸው” ብለዋል።

    ባለፈው ሳምንት በመካከለኛው ምሥራቅ ጉብኝት ላይ የነበሩት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ፤ ከጉዟቸው ሲመለሱ ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ ዋሽንግተን “አሁንም ከኢራን ጋር ለሚደረግ ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ በሯ ክፍት” መሆኑን ተናግረው ነበር።

    “ሁሌም ለዲፕሎማሲ ክፍት የሆንን ይመስለኛል። [መፍትሔው ግን] እውነተኛ መሆን አለበት። ልንገዛበት ፈቃደኛ የምንሆነው መሆን አለበት” ብለዋል።

    ኢራን ሰኔ ላይ ለተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት እንዳልተገዛች በመጥቀስ የከሰሱት ሩቢዮ፤ ሆርሙዝ ክፍት መሆን እንደነበረበት እንዲሁም በወሽመጡ የሚጓዙ መርከቦች ከጥቃት እና ከክፍያ ነጻ መሆን እንደነበረባቸው ገልጸዋል።

    አሜሪካ ለዲፕሎማሲ ክፍት ስለመሆኗ የተነሳላቸው የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ፣ “አሜሪካ ዲፕሎማሲ የምትለው ማስገደድ፣ ማስፈራራት፣ ዛቻ እና ማዕቀብ ነው” በማለት ተችተዋል።