በአሜሪካ “የስደተኞች ፖሊስ ተቃዋሚ” የሆነ የቀድሞ ወታደር በጸጥታ መሥሪያ ቤት ደጅ እሳት አሰነሳ

የፎቶው ባለመብት, Robert Sullivan/AP
በአሜሪካ ኒው ዮርክ ከተማ ውስጥ በሚገኝ የፌደራል ሕንፃ ፊት ለፊት እሳት ያስነሳ የቀድሞ ወታደር በቁጥጥር ሥር ዋለ።
ግለሰቡ ሰኞ ዕለት እሳት ያስነሳው የፌደራል የምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ)፣ የስደተኞች እና ጉምሩክ ደንብ አስከባሪ (አይስ) እንዲሁ የአሜሪካ ዜግነት እና ኢሚግሬሽን አገልግሎት ተቋማት የሚገኙበት ’26 ፌደራል ፕላዛ’ የተሰኘው ሕንፃ ደጅ ላይ ነው።
አንድሪው አራባካ የተባለው የ43 ዓመት ግለሰብ በአየር ግፊት የሚሰራ ፔሌት ሽጉጥ እንደተኮሰ እና ርችት እንደለኮሰ ተገልጿል።
የፌደራል የጸጥታ አባላት ቆንጨራ እና ሌሎች መሣሪያዎችን ይዞ የነበረውን ይህን ተጠርጣሪ ይዘውታል።
በዚህ ክስተት ማመልከቻው እየታየ የነበረ አንድ ስደተኛን ጨምሮ ሦስት ሰዎች ቀላል ጉዳት እንደደረሰባቸው ኤፍቢአይ ገልጿል።
የአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት፤ ግለሰቡን “ፀረ አይስ አማጺ” ሲል ጠርቶታል። እሳቱን ከማያያዙ በፊት በሕንፃው መግቢያ ደረጃዎች ላይ ማቀጣጠያ በማፍሰስ እሳት ማስነሳቱንም ጠቅሷል።
ቢቢሲ ስለ ጉዳዩ አስተያየት ለማግኘት ለአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት ጥያቄ አቅርቧል።
የእሳት አደጋ ባለሙያዎች እሳቱን አጥፍተውታል።
ኤፍቢአይ እንደሚገልጸው፤ ግለሰቡ "በክስተቱ ወቅት በርካታ መንግሥትን እና አይስን የሚቃወሙ ንግግሮችን” አሰምቷል።
በኤፍቢአይ የኒው ዮርክ ምክትል ዳይሬክተር ጄምስ ባርናክል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ አራባካ ሁለት መጥረቢያ፣ አንድ ቆንጨራ፣ ሦስት ቢላ እና ርችት ይዞ እንደነበር ተናግረዋል።
በያዘው የፔሌት ሽጉጥ ከአምስት እስከ ሰባት ጊዜ ወደ ሕንፃው አቅጣጫ እንደተኮሰም አስረድተዋል።










