የኢራን ጠቅላይ መሪ ለአባታቸው ግድያ “የበቀል እርምጃ” እንደሚወሰድ ተናገሩ

የፎቶው ባለመብት, Tasnim News Agency
የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ በጽሑፍ ባስተላለፉት መልዕክት አባታቸው ላይ ለተፈጸመው ግድያ “የበቀል እርምጃ” መወሰድ እንዳለበት አሳሰቡ።
የቀድሞው ጠቅላይ መሪ አያቶላህ ዓሊ ኻሜኒ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት በከፈቱበት የመጀመሪያው ቀን መገደላቸው ይታወሳል።
የአባታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ለተገኙ ሰዎች ምስጋና ያቀረቡት ሞጅታባ ኻሜኒ “ንጹህ ደምን ለመበቀል ቃል እንገባለን” ብለዋል።
“ወንጀለኛ እና የተዋረዱ ገዳዮች በከፈቷቸው ሁለት ጦርነቶች ለተገደሉ ሰማዕታትም የበቀል እርምጃ ይኖራል” ሲሉም አክለዋል።
አዲሱ ጠቅላይ መሪ “ይህ በቀል የአገራችን ፍላጎት ነው። እንደምንፈጽመው ጥርጥር የለም” ብለዋል።
የአባታቸው አያቶላህ ዓሊ ኻሜኒን ግድያ ተከትሎ አዲሱ ጠቅላይ መሪ ኃላፊነቱን ተረክበዋል።
እስካሁን ድረስ በይፋ ያልታዩ ሲሆን በቪድዮ እና በድምጽም መልዕክት አላስተላለፉም።
በአባታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ያልተገኙት ሞጅታባ ኻሜኒ መልዕክት የሚያደርሱት በጽሑፍ ብቻ ነው።























