አንዲ በርንሃም የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኑ
አንዲ በርንሃም በፈቃዳቸው ከሥልጣን የለቀቁትን የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር ተክተው የአገሪቱ መሪ ሆኑ።
የግሬተር ማንችስተር ከንቲባ የነበሩት በርንሃም፣ ዩናይትድ ኪንደግም ለመምራት በአምስት ዓመታት ውስጥ የተሾሙ ስድተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል። በአስር ዓመት ውስጥ ደግሞ ሰባተኛው የአገሪቱ መሪ ናቸው።
አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በመጀመሪያ ንግግራቸው፤ “አገራችን ውስጥ የሚታየው የጎዳና አዳር እንዲያበቃ [አደርጋለሁ]” ብለዋል።
ይህንን ለማስፈጸምም በአምስት ዓመታት ውስጥ ተጨማሪ 340 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚመደብ ተገልጿል።
በዚህ ገንዘብ አማካኝነት 1,200 ቤቶች እንደሚገነቡ እንዲሁም በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ቢያንስ ለ3,000 ሰዎች “ከፍተኛ ድጋፍ” እንደሚደረግ ጽሕፈት ቤታቸው አስታውቋል።
በርንሃም፤ መንግሥታቸው “ለሰዎች ውድቀት ከመክፈል ይልቅ፣ ስኬታቸው ላይ ኢንቨስት” እንዲያደርግ እንደሚፈልጉ በንግግራቸው ጠቅሰዋል።
በተያዘው 2026 መጨረሻም አገሪቱ የምትመራበት አዲስ የ10 ዓመት ዕቅድ ይፋ እንደሚደረግ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ "የሕይወት መሠረታዊ ፍላጎቶችን በሕዝብ ቁጥጥር ስር ማድረግ" የሚያስችል ኢኮኖሚ እንደሚገነቡም ተናግረዋል።
ከአውሮፓውያን 2016 ወዲህ የተሾሙ ሰባተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር መሆናቸውን በደንብ እንደሚገነዘቡ በመጥቀስም፤ “መለስ ብሎ መመልከቻ እና አዲስ ውሳኔ” ላይ መድረሻ ጊዜ እንዲኖር ጥሪ አቅርበዋል። ብሪታኒያ መረጋጋት ማግኘት እንዳለባትም በአጽንኦት አንስተዋል።
ፖለቲከኞች “በበቂ ሁኔታ ጥሩ አልነበሩም” በማለት የተቹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የተሻለ ለመሆን ቃል ገብተዋል። ባለፉት 40 ዓመታት ውስጥ ያልታዩ ከፍተኛ ለውጦችን እንደያደርጉም ተናግረዋል።