ሰበር, ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ባሕር ኃይል የሆርሙዝ ወሽመጥን እንዲዘጋ አዘዙ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ባሕር ኃይል ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች እንቅስቃሴን እንዲያግድ ማዘዛቸውን አስታወቁ።
በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ለረጅም ሰዓታት ፓኪስታን ውስጥ የተካሄደው ድርድር ውጤት ሳያስገኝ ከቀረ በኋላ ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ረዘም ያለ ጽሁፍ ላይ በአንዳንድ ነጥቦች ላይ ስምምነት መደረሱን አመልክተዋል።
"ውይይቱ በጥሩ ሁኔታ ተከናውኖ በአብዛኞቹ ነጥቦች ላይ ስምምነት ላይ ተደርሷል፤ ነገር ግን እጅግ አስፈላጊ በሆነው በኒውክሌር ጉዳይ ላይ ግን መስማማት አልተደረሰም” ብለዋል።
ጨምረውም በሆርሙዝ በኩል የሚደረግ ነጻ እንቅስቃሴን በሚመለከት ከስምምነት ሊደረስ እንሚችል አመልክተው፤ ነገር ግን “ኢራኖች ከእነሱ ውጪ ማንም የማያውቃቸው ‘በባሕሩ የተወሰኑ ቦታዎች ላይ ፈንጂዎች ሊኖሩ ይችላሉ’ በማለት ፈቃደኛ አልሆኑም” ሲሉ አስፍረዋል።
ስለዚህም ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ባሕር ኃይላችን በዓለም አቀፍ የውሃ አካል ላይ ለኢራን የመተላለፊያ ገንዘብ የከፍሉ መርከቦችን እንዲያስቆም” ማዘዛቸውን እና ባሕር ኃይላቸው “በኢራን የተጠመዱ የባሕር ላይ ፈንጂዎችን ማስወገድ ይጀምራል” ብለዋል።
“ሕገወጥ የመተላለፊያ ክፍያውን የፈጸመ የትኛውም መርከብ እንዲያልፍ አይፈቀድለትም” በማለት “በእኛ ላይ ወይም በሰላማዊ መርከቦች ላይ የሚተኩስ ማንኛውም ኢራናዊ መአት ይወርድበታል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
የሆርሙዝ ወሽመጥ በአሜሪካ ባሕር ኃይል በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚዘጋም ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስታውቀዋል።


















