ቀጥታ, አሜሪካ በኢራን ጦርነት እስካሁን 25 ቢሊዮን ዶላር ማውጣቷን አስታወቀች

ኢራን ላይ የተከፈተው ጦርነት እስካሁን ድረስ አሜሪካን 25 ቢሊዮን ዶላር እንዳስወጣት የዋሽንግተን መከላከያ መስሪያ ቤት ከፍተኛ ኃላፊ ተናገሩ። ሁለት ወር ባለፈው የኢራን ጦርነት አሜሪካ ምን ያህል ገንዘብ ወጪ እንዳደረገች በይፋ ሲገለጽ ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ዴሞክራት ሕግ አውጪዎች ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት የፌደራል መንግሥቱ ገንዘብ ጥቅም ላይ እየዋለ የሚገኝበትን መንገድ ተችተዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ለማስከፈት የዓለም አቀፍ ድጋፍ ትፈልጋለች ተባለ

    አሜሪካ ሌሎች አገራት ዓለም አቀፍ ጥምረት እንዲመሠርቱ እና የሆርሙዝ ወሽመጥን እንዲያስከፈቱ እንደምትፈልግ ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የዜና ወኪሉ የተመለከተው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰነድ የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ የሚተላለፍበት ወሽመጥን ዳግም ለመርከቦች ክፍት እንዲሆን ለማድረግ አገራት ዓለም አቀፍ ጥምረት እንዲመሰርቱ ግፊት እያደረገች መሆኑን ያሳያል።

    ሁለት ወር ባለፈው በኢራን ጦርነት ምክንያት የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ከአራት ኣመታት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ጭማሪ አሳይቷል።

    ጦርነቱን ለማስቆም የተደረጉ ንግግሮች ውጤት ባለማስገኘታቸው አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እገዳ ጥላለች።

    የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሐሙስ ዕለት ኢራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንድትመለስ ለማድረግ የሚያስችል ወታደራዊ ዕቅድ ላይ ለፕሬዚዳንቱ ገለጻ እንደሚደረግ አክሲዮስ ዘግቧል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ “አጭር እና ከባድ” የሆነ የጥቃት እቅድ ለፕሬዚዳንቱ እንደሚያቀርብ የተገለጸ ሲሆን በዚህ ጥቃት ምናልባት የኢራን መሠረተ ልማቶች ዒላማ ሊደረጉ እንደሚችሉ አክሲዮስ በስም ያልጠቃሳቸውን ምንጮች ጠቅሶ ዘግቧል።

    ዋይት ሐውስ እና ማዕከላዊ ዐዕዙ ሮይተርስ ላቀረበው ጥያቄ ምላሸ አልሰጡም።

  2. እስራኤል እርዳታ ይዘው ወደ ጋዛ ሲጓዙ የነበሩ መርከቦችን ጠልፋ፤ 175 አክቲቪስቶችን አሰረች

    ለጋዛ እርዳታ ጭነው ሲጓዙ የነበሩ 22 ጀልባዎች በግሪኳ ክሪት ደሴት አቅራቢያ ዓለም አቀፍ ውሃ ላይ ሳሉ በእስራኤል ኃይሎች መጠለፋቸውን የፍልስጤም ደጋፊ አክቲቪስቶች አስታወቁ።

    የመርከቦቹን የቡድን ጉዞ ያቀናጀው ‘ግሎባል ሱሙድ ፍሎቲላ’ የተባለው ተቋም የእስራኤልን እርምጃ “የባሕር ላይ ውንብድና” ሲል ተቃውሞታል።

    መርከቦቹ ላይ የነበሩት ሰዎች በእስራኤል ባሕር ኃይል ከተዘጋው ጋዛ 965 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ መያዛቸውን ተቋሙ ገልጿል።

    የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ ከ20 በሚበልጡ ጀልባዎች ውስጥ የነበሩ 175 አክቲቪስቶችን መያዙን እና ወደ እስራኤል እየተወሰዱ መሆኑን አስታውቋል። የጀልባዎቹን ጉዞም “የሕዝብ ግንኙነት ትርኢት” ሲል አጣጥሎታል።

    እስራኤል ጋዛ ላይ የጣለችውን እገዳ የመስበር እቅድ በመያዝ ከሁለት ሳምንት በፊት የሕብረት ጉዞ የጀመሩት ከስፔን፣ ፈረንሳይ እና ጣልያን የተወጣጡ 58 መርከቦች ናቸው።

    የ‘ግሎባል ሱሙድ ፍሎቲላ’ መረጃ እንደሚያሳየው ቀሪዎቹ 36 ጀልባዎች በደቡብ ምዕራባዊ የክሪት ባሕር ዳርቻ አቅራቢያ እየቀዘፉ ነበር።

    የቡድኑ አባላት ከነበሩት መርከቦች ውስጥ ቢያንስ 22 ያህሉ “ሙሉ በሙሉ የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት በሆነ መልኩ በእስራኤል ኃይሎች መወረራቸውን” ተቋሙ ገልጿል።

    የእስራኤል ባሕር ኃይል “መርከቦችን እንደጠለፈ፣ የአደጋ ጊዜ ቻናሎችን ጨምሮ የኮሚዩኒኬሽን መስመራቸውን እንደጠለፈ እና ሲቪል ሰዎችን በኃይል አፍኖ እንደወሰደ” በመግለጫው ጠቅሷል።

    “ይሄ የባሕር ላይ ውንብድና ነው። በክሪት አቅራቢያ ክፍት ውሃ ላይ ሰዎችን በሕገ ወጥ መንገድ መያዝ እስራኤል ከራሷ ድንበር ሩቅ የሆነ ስፍራ ላይ ያለ ምንም ተጠያቂነት፣ ያለ ምንም መዘዝ እንደምትንቀሳቀስ ያመለክታል” ብሏል።

    የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ዘገባዎች በበኩላቸው የባሕር ኃይሉ ለመርከቦቹ ማስጠንቀቂያ እንደሰጠ እና ትዕዛዙን ያልተቀበሉትን እንደያዘ ገልጸዋል። እስራኤል እርምጃዋ ዓለም አቀፍ ሕግን ያከበረ እንደሆነ ትናገራለች።

  3. የነዳጅ ዋጋ ከአራት ዓመት ወዲህ ባልታየ መጠን ጨመረ

    አሜሪካ እና ኢራን ከሁለት ወር በፊት የገቡበት ጦርነት የመቋጨት አዝማሚያ እያሳየ አለመሆኑን ተከትሎ በዓለም አቀፍ ገበያ የነዳጅ ዋጋ ከአውሮፓውያኑ 2022 ወዲህ ባልታየ መጠን ጨመረ።

    የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋው በሰባት ፐርሰንት ገደማ ጨምሮ በበርሜል ከ126 ዶላር በላይ ተሽጧል። አሁን የተመዘገበው የነዳጅ ዋጋ ሩሲያ ዩክሬን ላይ ሙሉ ወረራ ከከፈተች ወዲህ የታየ ከፍተኛ ጭማሪ ሆኗል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የሚደረገው የሰላም ንግግር ያለ ተጨባጭ እንቅስቃሴ ባለበት መቆሙን ተከትሎ የኤነርጂ ዋጋ በዚህ ሳምንት ጨምሯል።

    በእስያ ገበያ ላይ የነዳጅ ዋጋ በበርሜል 126.32 ዶላር የተሸጠ ሲሆን የአውሮፓ ገበያ ሲከፈት ግን የብሬንት ዋጋ ወደ 122 ዶላር ተመልሷል።

    ቤንዚን እና ናፍጣ የሚገኝበት ድፍድፍ ነዳጅ ከኢራን ጦርነት ጀመር ወዲህ ያሳየው ጭማሪ የነዳጅ ችርቻሮ ዋጋ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል።

    ረቡዕ ዕለት አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የጣለችውን እገዳ ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋት እስከቀጠች ድረስ ለማራዘም መዘጋጀቷ ከተዘገበ በኋላም የነዳጅ ዋጋ በስድስት በመቶ ጨምሮ ታይቷል።

  4. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ላይ ሊወሰድ ስለሚችል ወታደራዊ እርምጃ ገለጻ ሊደረግላቸው መሆኑ ተዘገበ

    የአሜሪካ ወታደራዊ አዛዦች ኢራን ውስጥ ሊፈጸሙ የሚችሉ “አጭር እና ኃይለኛ” ተከታታይ ጥቃቶችን የተመለከተ እቅድ ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሊያቀርቡ መሆኑን የአሜሪካው የዜና ምንጭ አክሲዮስ ዘገበ።

    አክሲዮስ ለጉዳዮ ቅርበት ያላቸው ምንጮችን ጠቅሶ ያወጣው ዘገባ እንደሚያመልክተው፤ የአሜሪካን መካከለኛው ምሥራቅ ዘመቻዎች የሚመራው ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ በሆኑት አድሚራል ብራድ ኩፐር የሚቀርበው እቅድ የኢራን መሠረተ ልማቶችን ማጥቃትን ሊያካትት ይችላል።

    የትራምፕ አስተዳደር ኢራን ላይ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድን እያጤነ ያለው ጥቃት መፈጸም ከቴህራን ጋር የሚደረገው ድርድርን ከገባበት ቅርቃር ያስወጣል በሚል ተስፋ መሆኑን ዘገባው ጠቅሷል።

    ኢራን ጥቃት ከተፈጸመባት ድርድሩ ላይ የኒውክሌር ጉዳይን በተመለከተ መለሳለስ ልታሳይ ትችላለች ተብሎ ተገምቷል።

    በዘገባው መሠረት ለትራምፕ ይቀርባል ሌላኛው እቅድ በኢራን የተዘጋውን ሆርሙዝ ለንግድ መርከቦች ክፍት ለማድረግ ሲባል የወሽመጡን የተወሰነ ክፍል መቆጣጠርን የሚመለከት ነው።

    ይህ አይነቱ እርምጃ እግረኛ ወታደሮችን ማሰማራትን ሊያካትት እንደሚችል አክሲዮስ አንድ ምንጭን ጠቅሶ ዘግቧል።

    በከፍተኛ መጠን የበለጸገውን የኢራን የዩራኒየም ክምችት ለመቆጣጠር በሠራዊቱ ልዩ ኃይል ዘመቻ የማካሄድ እቅድም ለፕሬዝዳንቱ ሊቀርብ ይችላል ተብሏል። ይህ አይነቱ እቅድ ከዚህ ቀደምም ተነስቶ ነበር።

    በአሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት የተከፈተባት ኢራን ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ ዘግታለች። በወሽመጡ ለማለፍ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም መዛቷንም ቀጥላለች።

    ይህ የኢራን እርምጃ የዓለም የኤነርጂ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ መስተጓጎል ያደረሰ ሲሆን አሜሪካ ደግሞ በምላሹ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ እገዳ ጥላለች።

    እንደ አክሲዮስ ዘገባ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን ወደቦች ላይ የጣሉትን የጉዞ እገዳ እንደ ትልቅ መደራደሪያ ይመለከቱታል። ይሁን እንጂ ኢራን በዚሁ አቋሟ የምትቀጥል ከሆነ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድን ሊያጤኑት እንደሚችሉ ጠቅሷል።

    በተጨማሪም ኢራን የአሜሪካ እገዳ የሚቀጥል ከሆነ በአጸፋው በቀጣናው የሚገኙ አሜሪካ ኃይሎች ላይ ወታደራዊ እርምጃ ልትወስድ ትችላለች የሚል ግምት መኖሩን የዜና ምንጩ ዘግቧል።

  5. የጀርመን መራሄ መንግሥት አሜሪካን ከተቹ ከቀናት በኋላ ትራምፕ በአገሪቱ የሰፈሩ ወታደሮችን ለመቀነስ እያሰቡ መሆኑ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጀርመን ውስጥ የሰፈሩትን በሺህዎች የሚቆጠሩ የአሜሪካ ወታደሮች ቁጥር ለመቀነስ “ጥናት እየተደረገ” መሆኑን አስታወቁ።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት፤ የጀርመኑ መራሄ መንግሥት ፍሬድሪክ መርዝ፤ አሜሪካ በኢራን ተደራዳሪዎች “ተዋርዳለች” በማለት የዋሽንግተንን አካሄድ ከተቹ ከቀናት በኋላ ነው።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ “ጀርመን ውስጥ ያሉ ወታደሮች ላይ ሊደረግ የሚችል ቅነሳን በተመለከተ በመጪው አጭር ጊዜ ውስጥ ምን አይነት ውሳኔ መተላለፍ እንዳለበት እያጠኑ እና እየገመገሙ” መሆኑን ገልጸዋል።

    አሜሪካ ጀርመን ውስጥ ከፍተኛ የሠራዊት አባላትን ያሰፈረች ሲሆን፣ እስከ ታህሳሥ ባለው ጊዜ ውስጥ በመላ አገሪቱ በሚገኙ ጦር ሰፈሮች 36,000 ወታደሮች እንደነበሯት መረጃዎች ያመለክታሉ።

    የጀርመኑ መራሄ መንግሥት መርዝ አሜሪካን የሚተቸውን ንግግራቸውን ያሰሙት ሰኞ ዕለት ማርስበርግ ውስጥ በሚገኝ ዩኒቨርሲቲ ተገኝተው ለተማሪዎች ባደረጉት ንግግር ነው። “አሜሪካ ምንም ስትራቴጂ እንደሌላት ግልጽ ነው” ሲሉ ለተማሪዎቹ ተናግረዋል።

    “ኢራናውያኑ ድርድር ላይ እጅግ የተካኑ መሆናቸው ወይም ድርድር አለማድረግ ላይ በጣም ጎበዝ መሆናቸው ግልጽ ነው። አሜሪካውያን ወደ ኢስላማባድ እንዲጓዙ እና ያለ ውጤት በድጋሚ እንዲመለሱ አድርገዋል” ብለዋል። “መላ አገሪቱ” በኢራን አመራር “እየተዋረደ” መሆኑንም አክለዋል።

    ትራምፕ በማግሥቱ ትሩዝ ሶሻል በተባለው ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በሰጡት ምላሽ፤ የጀርመኑ መሪ “ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ ቢኖራት ችግር የለበትም”፤ እንዲሁም “ስለ ምን እንደሚናገር አያውቅም” ሲሉ ተችተዋል።

    “ጀርመን በኢኮኖሚ እና በሌሎች ጉዳዮች ደካማ መሆኗ አያስገርምም” ሲሉ ጽፈዋል።

    ረቡዕ ዕለት ከትራምፕ ጋር ስላላቸው ግንኙነት የተጠየቁት መርዝ፣ “በእኔ እና በአሜሪካው ፕሬዝዳንት መካከል ያለው ግላዊ ግንኙነት እንደቀደመው ጊዜ ሁሉ ጥሩ ላይ ነው” ብለዋል።

    ትራምፕ ጀርመን ውስጥ የሚገኙ ወታደሮችን ቁጥር እንደሚቀንሱ ስለመጠቆማቸው እስካሁን አስተያየት አልሰጡም።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ባለፉት ሁለት ወራት 23 አባላት ካሉት እና “የወረቀት ላይ ነብር” ሲሉ ካጣጣሉት ኔቶ አሜሪካን እንደሚያስወጡ ሲዝቱ ቆይተዋል።

  6. አሜሪካ በኢራን ጦርነት እስካሁን 25 ቢሊዮን ዶላር ማውጣቷን አስታወቀች

    ከሁለት ወር በፊት ኢራን ላይ የተከፈተው ጦርነት እስካሁን አሜሪካን 25 ቢሊዮን ዶላር እንዳስወጣት የዋሽንግተን መከላከያ መስሪያ ቤት ከፍተኛ ኃላፊ ተናገሩ።

    አሜሪካ በኢራን ጦርነት ምን ያህል ገንዘብ ወጪ እንዳደረገች በይፋ ሲገለጽ ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚንስትር ፒት ሄግሴት ከኢራን ጦርነት ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በቃለ መሃላ ስር ሆነው በሰጡት ስድስት ሰዓት በቆየ የምክር ቤት ማብራሪያ ላይ ከዴሞክራቲክ ሕግ አውጪዎች ጋር ውዝግብ ውስጥ ገብተዋል።

    መከላከያ ሚንስትሩ ትናንት ረቡዕ በተወካዮች ምክር ቤት የጦር አገልግሎት ኮሚቴ ፊት የቀረቡት ከአሜሪካ ጦር የጋራ ጦር አዛዦች ኃላፊ ጄነራል ዳን ኬን እና ከመከላከያ መስሪያ ቤቱ የፋይናንስ ዋና ኃላፊ ጁሌስ ኸርትስ ጋር በመሆን ነው።

    ሄግሴት ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር “የተጋፈጥነው ትልቁ ጠላት” የዴሞክራቶች እና የተወሰኑ ሪፐብሊካኖችን “የሽንፈት ቃላቶች ነው” ብለዋል።

    የኮሚቴው አባል የሆኑ ዴሞክራት ሕግ አውጪዎች ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት የፌደራል መንግሥቱ ገንዘብ ጥቅም ላይ እየዋለ የሚገኝበትን መንገድ ተችተዋል።

    ከመከላከያ መስሪያ ቤቱ የፋይናንስ ዋና ኃላፊ ኸርትስ ባደረጉት ንግግር እስካሁን ለጦርነቱ 25 ቢሊዮን ዶላር ወጪ መደረጉን ተናግረዋል።

    ኸርትስ እንደገለጹት አብዛኛው ገንዘብ የወጣው ለተተኳሽ እና መሣሪያዎችን ለመተካት ነው። የወጪው ሙሉ ዝርዝር ከጊዜ በኋላ እንደሚቀርብ ለሕግ አውጪዎች ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን የሰላም ንግግር ለማድረግ ተኩስ አቁም ላይ ቢደርሱም ጦርነቱ በይፋ አልተቋጨም።

    በምክር ቤቱ ውሎ ዋነኛ መነጋገሪያ ከሆኑ ነጥቦች አንዱ ገንዘብ ነው። ዋይት ሀውስ የአሜሪካ የመከላከያ በጀት በ1.5 ትሪሊዮን ዶላር እንዲጨምር ለኮንግረስ ጥያቄ አቅርቧል።

    ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ የአሜሪካ ወታደራዊ ወጪ በዚህ ደረጃ ከፍ ሲል ይህ የመጀመሪያው ነው።

    መከላከያ ሚንስትሩ ሄግሴት የበጀት ጥያቄው “ጊዜው የሚጠይቀውን አጣዳፊነት ያሳያል” ሲሉ ለኮሚቴው ተናግረዋል።

    ጄነራል ኬን በበኩላቸው 1.5 ትሪሊዮን ዶላር አሜሪካ በፍጥነት የሚያድግ ቴክኖሎጂ መታጠቅ እንድትችል የሚያግዝ “ለወደፊት ደኅንነት የሚውል ታሪካዊ ቅድመ ክፍያ” ነው ብለዋል።

    የኮሚቴው አባላት የሆኑ ዴሞክራቶች የአሜሪካ ጦር ኢራን ላይ የሚያካሂደውን ዘመቻ ብዙውን ጊዜ የሚገልጹት ያለ ኮንግረስ ፈቃድ እንደተከፈተ “የምርጫ ጦርነት” ነው።

    የካሊፎርኒያው ዴሞክራቲክ ተወካይ ጆን ጋራሜንዲ፤ “ጦርነቱን በተመለከተ ከመጀመሪያው ዕለት አንስቶ የአሜሪካ ሕዝብን ስትዋሹ ነበር” ሲሉ ባለሥልጣናቱን ወቅሰዋል።

    ትራምፕ በሌላ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት “አጣብቂኝ ውስጥ ገብተዋል” ሲሉም ለሄግሴት ተናግረዋል።

    የምክር ቤት አባሉን አስተያየት “ግድ የለሽ” ሲሉ የጠሩት ሄግሴት በበኩላቸው፤ ትራምፕ “አጣብቂኝ” ውስጥ ናቸው መባሉን አስተባብለዋል። “ለትራምፕ ያለህ ጥላቻ አውሮሃል” ሲሉም የምክር ቤት አባሉን ተናግረዋል።

    የኮሚቴው አባል የሆኑ አብዛኞቹ ሪፐብሊካኖች ከመከላከያ መስሪያ ቤቱ ጎን ቆመዋል። የኮንግረስ አባሉ ካርሎስ ጊሜኔዝ ኢራን የህልውና ስጋት ናት ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል።

  7. የዚምቧብዌ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ ልጅ ከደቡብ አፍሪካ ሊባረር ነው

    የዚምባብዌ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ የመጨረሻ ልጅ በአስቸኳይ ከደቡብ አፍሪካ እንዲባረር የጆሃንስበርግ ፍርድ ቤት ወሰነ።

    ቤላርማይን ሙጋቤ በዚህ ወር መጀመርያ ላይ በመኖሪያ ቤቱ የ23 ዓመት ወጣት ላይ በመተኮሱ የተከሰሰ ሲሆን ጥፋተኛ መሆኑን አምኗል።

    የ28 ዓመቱ የሙጋቤ ልጅ መሳሪያ በመደቀን እንዲሁም በደቡብ አፍሪካ ውስጥ ያለ ሕጋዊ ፈቃድ በመኖር ጥፋተኛ መሆኑ ተገልጿል።

    ፍርድ ቤት በቀረበበት ክስ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ 36,000 ዶላር እንዲከፍል ወስኖበታል።

    አብሮት የተከሰሰው የአጎቱ ልጅ ቶቢያስ ማቶንሆድዜ በግድያ ሙከራ፣ በሕገወጥ ስደት፣ የጦር መሣሪያ በመያዝ እና በፍትህ ስርዓቱ ላይ ጣልቃ በመግባት ወንጀሎች የሦስት ዓመት እስር ተፈርዶበታል።

    ሁለቱም ግለሰቦች በቁጥጥር ስር የዋሉት ከአስር ቀን በፊት ፖሊስ በጆሃንስበርግ በሚገኘው የሙጋቤ ልጅ ቤት ተጠርቶ ከመጣ በኋላ ነው።

    በቅጥር ግቢው ውስጥ ይሰራ የነበረው ግለሰብ በጥይት ተመትቶ ክፉኛ በመጎዳቱ ወደ ሆስፒታል ተወስዷል።

    አቃቤ ሕጎች ለፍርድ ቤቱ ግለሰቡ ላይ የተተኮሰው በቅጥር ግቢው ውስጥ ሦስት ሰዎች መካከል በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን አስረድተዋል።

    አክለውም ግለሰቡ ለማምለጥ ሲሞክር ከኋላው ሁለት ጊዜ ተተኩሱበት መመታቱን ገልጸዋል።

    ፖሊስ የመኖሪያ ቤቱ ላይ ብርበራ ያካሄደ ቢሆንም እስካሁን ድረስ የጦር መሣሪያውን አላገኘም።

  8. በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለው እገዳ እንደሚራዘም ከተሰማ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን እገዳ ለማራዘም ማቀዷ ከተሰማ በኋላ የዓለም ነዳጅ ዘይት ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ጨመረ።

    ማክሰኞ ዕለት 110 ዶላር የተሸጠው አንድ በርሜል ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ረቡዕ 115 ዶላር ገብቷል።

    የነዳጅ ዋጋ የጨመረው ዎል ስትሪት ጆርናል ዶናልድ ትራምፕ የኢራን ምጣኔ ሃብትን ለማዳከም በቴህራን ወደቦች ላይ የተጣለውን እገዳ እንደሚያራዝሙ ለረዳቶቻቸው መናገራቸውን ከዘገበ በኋላ ነው።

    ኢራን የአሜሪካ እገዳ እስካልተነሳ ድረስ በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች እንደማያልፉ ተናግራለች።

    የካቲት 21 2018 ዓ.ም. እስራኤል እና አሜሪካ ኢራንን መደብደብ ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የዓለም ነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

    ኢራን ለተከፈተባትን ጦርነት ምላሽ ለመስጠት በሚል የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ምርት የሚመላለስበት የሆርሙዝ ወሽመጥን ዘግታለች።

  9. ፈረንሳይ ዜጎቿ በፍጥነት ማሊን ለቅቀው እንዲወጡ አሳሰበች

    የማሊ ታጣቂዎች በሳምንቱ መጨረሻ የተቀናጀ ጥቃት መክፈታቸውን ተከትሎ ፈረንሳይ ዜጎቿ “በተቻለ ፍጥነት” አገሪቱን ለቅቀው እንዲወጡ አሳሰበች።

    ቅዳሜ ዕለት በማሊ ተገንጣይ ቡድኖች እና እስላማዊ ታጣቂዎች በጋራ በመሆን በከፈቱት ጥቃት ዋና ከተማዋ ባማኮን ጨምሮ በበርካታ የአገሪቱ ክፍል ውጊያ ተካሄዷል።

    ፈረንሳይ ረቡዕ በማሊ ያለው ሁኔታ “ፈጽሞ ያልተረጋጋ” መሆኑን በመግለጽ ዜጎቿ ወደ ምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር እንዳይሄዱ መክራለች።

    የማሊ የመከላከያ ሚኒስትር በዋና ከተማዋ ባማኮ አቅራቢያ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው መኪና ላይ በተጠመደ ቦምብ በተፈጸመ ጥቃት መገደላቸው ተገልጿል።

    ሳዲዮ ካማራ የተገደሉት እስላማዊ ታጣቂዎች እና ተገንጣዮች በመላ አገሪቱ በከፈቱት የተቀናጁ የጥቃት ማዕበሎች መሆኑን የበርካታ የዜና አውታሮች ዘገባ አመልክቷል።

    የማሊ ጦር ጄነራል አሲሚ ጎይታ የአገሪቱ ጸጥታ መረጋጋቱን በትናንትናው ዕለት አስታውቀዋል።

    ማክሰⶉ ምሽት የአገሪቱ ጦር በታጣቂዎች ላይ “ከፍተኛ ኪሳራ” ማድረሱን ገልጾ አሁንም ዘመቻ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁሟል።

  10. እስራኤል በደቡብ ሊባኖስ በፈጸመችው ተከታታይ ጥቃት ሦስት የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ተገደሉ

    እስራኤል በደቡብ ሊባኖስ በፈጸመችው ሁለት ተከታታይ ጥቃት ሦስት የአደጋ ጊዜ ሠራተኞችን ጨምሮ አምስት ሰዎች መገደላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ጥቃቱን “የጦር ወንጀል” ሲሉ ኮንነውታል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር በመጀመርያው የእስራኤል ጥቃት የተጎዱ ሰዎችን ለማትረፍ የተላኩ ሦስት የአገሪቱ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በሁለተኛው ጥቃት መገደላቸውን አስታውቋል።

    በኋላ ላይ የሞታቸው መንስዔ ሲጣራ በፍርስራሸሶች ውስጥ ተቀብረው ሕይወታቸው ማለፉ ተረጋግጧል።

    ሚኒስቴሩ ሁለቱ የተገደሉት ሰዎች ማን እንደሆኑ ይፋ አላደረገም። በጥቃቱ ሁለት የሊባኖስ ጦር ወታደሮች ጉዳት እንደደረሰባቸውም ታውቋል።

    የእስራኤል ጦር ስለጥቃቱ ጥያቄ ቢቀርብለትም ምላሽ ከመስጠት ተቆጥቧል።

    የሰብዓዊ መብቶች ብድኖች በሕክምና ባለሙያዎች ላይ ሆን ተብሎ የሚፈጸም ጥቃት ከጦር ወንጀል ጋር ይስተካከላል ብለዋል።

    በእስራኤል እና ሄዝቦላህ መካከል ዳግም ግጭት የተቀሰቀሰው የኢራን ጦርነትን ተከትሎ ወደ ቴል አቪቭ ሮኬቶችን ማስወንጨፍ በመጀመሩ ነው።

    እስራኤል እና ሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ቢደርሱም፣ በደቡባዊ ሊባኖስ የእግረኛ ጦሯን አሰማርታ መጠነ ሰፊ ወታደራዊ ዘመቻ እያካሄደች ትገኛለች።

    በእስራኤል ጦር በተፈጸሙ ጥቃቶች እስካሁን ድረስ 103 የሕክምና ባለሙያዎችን ጨምሮ 2500 ሰዎች ተገድለዋል።

    ከሟቾቹ መካከል 270 ሴቶች እና ከ 170 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ሕጻናት መሆናቸው ተገልጿል።

  11. ትራምፕ ኢራን አቋሟን አስተካክላ የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለመተው መስማማት አልቻለችም ሲሉ ተቹ

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ ረቡዕ ዕለት የኢራን አመራሮች “በተቻለ ፍጥነት ብልህ ቢሆኑ” እና የኒውክሌር ፕሮግራማቸውን ለመተው ቢስማሙ እንደሚሻል ተናገሩ።

    በኢራን እና በአሜሪካ መካከል የተጀመረው ጦርነት ሁለት ወር አልፎታል።

    “ኢራን አቋማቸውን ማስተካከል አትችልም። የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለመተው እንዴት መስማማት እንዳለባት አታውቅም” ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ትራምፕ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ከምስላቸው ጋር ባጋሩት በዚህ ልጥፍ ከጀርባቸው ቤቶች እየፈነዱ እርሳቸው ኤኬ-47 ጠብመንጃ ይዘው ይታያሉ።

    በምስሉ ላይ “ከእንግዲህ በኋላ ትዕግሥት የለም” የሚል ጽሑፍ ተካትቷል።

    ዋይት ሐውስ ከኢራን ጋር በኒውክሌር ፕሮግራሞቿ ላይ ለመነጋገር ቢሞክርም ቴህራን ግን ፈቃደኛ ሳትሆን ቀርታለች።

    ቴህራን በቅድሚያ የሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት የጠየቀች ሲሆን በኒውክሌር ፕሮግራሟ ላይ የሚደረገው ንግግር ወደ ሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ መጠየቋ ተዘግቧል።

    ትራምፕ ወደ ኢራን የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች እንቅስቃሴ ላይ እገዳ መጣላቸው ይታወሳል።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል የአሜሪካው ፕሬዚዳንት እገዳው እንዲራዘም መወሰናቸውን ዘግቧል።

  12. የቀድሞ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ፔንታጎን በኢራን ትምህርት ቤት ላይ ስለተፈጸመው ጥቃት ዝም ማለቱን ተቹ

    አምስት የቀድሞ የአሜሪካ ባለሥልጣናት በኢራን ጦርነት መጀመሪያ ላይ በትምህርት ቤት ላይ በተፈጸመ ጥቃት የአሜሪካ ጦር ስለነበረው ተሳትፎ ባለመግለጹ ፔንታጎንን ተቹ።

    ከእነዚህ ባለሥልጣናት መካከል አንዳንዶቹ ጥቃቱ ከተፈጸመ ረጅም ጊዜ በኋላ እንኳን መሠረታዊ ዝርዝሮች ይፋ አለመሆናቸው በጣም ያልተለመደ መሆኑን ተናግረዋል።

    የካቲት 21 2018 ዓ.ም. በሚናብ በሚገኝ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርት ቤት ላይ በተፈጸመ የሚሳዔል ጥቃት 110 ሕጻናትን ጨምሮ 168 ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    ከዚያን ጊዜ ወዲህ ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ ፔንታጎን ክስተቱ በምርመራ ላይ መሆኑን ብቻ አስታውቋል።

    የአሜሪካ ሚዲያዎች በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ የአሜሪካ ጦር መርማሪዎች የአሜሪካ መከላከያ ትምህርት ቤቱን ባለማወቅ በመምታታቸው ተጠያቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ቢያምኑም የመጨረሻ መደምደሚያ ላይ አለመድረሳቸውን ዘግበዋል።

    ቢቢሲ ስለ ጥቃቱ እና ግልፅነት ባለመኖር ላይ ስለሚቀርበው ክስ ለፔንታጎን ባለሥልጣን ጥያቄ አቅርቦ "ይህ ክስተት በአሁኑ ጊዜ በምርመራ ላይ ነው" የሚል ምላሽ አግኝቷል።

    ባለሥልጣኑ አክለውም ተጨማሪ ዝርዝሮች እንደተገኙ ይፋ እንደሚደረጉ ተናግረዋል።

    ቢቢሲ በአሜሪካ ወታደራዊ ዘመቻዎች ወቅት ሰላማዊ ዜጎች የተገደሉባቸውን ሦስት ጉዳዮችን ፈትሿል።

    በእያንዳንዱ ጥቃት ላይ ፔንታጎን ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ ዝርዝር መረጃዎችን ሰጥቷል።

  13. የኢራንን ሥልጣን በበላይነት የተቆጣጠረው አብዮታዊ ዘብ

    ለሁለት ወራት በዘለቀው የኢራን ጦርነት ቴህራን አንድ የማያሻማ መመሪያ የሚሰጥ ሃይማኖታዊ መሪ የላትም።

    ይህ በድንገት ፍጻሜውን ያገኘው የኢራን አገዛዝ የአገሪቱ ዕጣ ፈንታ በአክራሪ የአብዮታዊ ዘብ አዛዦች እጅ እንዲወድቅ አድርጓል።

    የእስላማዊ ሪፐብሊክ እአአ በ1979 ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ በቁልፍ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻውን ውሳኔ የሚሰጡት ጠቅላይ መሪው ነበሩ። ነገር ግን የአያቶላህ አሊ ኻሜኒ መገደል እና እርሳቸውን ተክቶ የልጃቸው ወደ ሥልጣን መምጣት የአብዮታዊ ዘቡ ጄነራሎች ውሳኔ ሰጪነት እንዲገን አድርጓል።

    በዚህ የተነሳ ደግሞ ወሳኝ የሆነው ውሳኔ ሰጭ አካል በመጉደሉ ሞጅታባ ኻሜኒ በአብዮታዊ ዘቡ አዛዦች ላይየበለጠ እንዲደገፉ አድርጓቸዋል።

    ሞጅታባ ኻሜኒ የሥርዓቱ ቁንጮ ላይ ናቸው። ነገር ግን ሦስት ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ የውስት አዋቂዎች ለሮይተርስ እንደተናገሩት ጠቅላይ መሪው ውሳኔያቸውን የሚሰጡት በአዛዦቹ ላይ በመመስረት ነው።

    የኢራን አመራር በጦርነቱ የተነሳ ውሳኔዎቹን በጥቂት ጠቅላይ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤቱ ባሉ አክራሪ ቡድኖች ላይ እንዲመሰረት አድርጎታል።

    ይህ ደግሞ በአሁኑ ወቅት ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ ውሳኔዎች ላይ ጫና ፈጥሯል። አንድ ከፍተኛ የፓኪስታን ባለሥልጣን “ኢራናውያን ምላሽ ሲሰጡ እጅግ በጣም ዝግ ብለው ነው” ብለዋል።

    “አንድ ወጥ የሆነ ውሳኔ ሰጭ መዋቅር የለም። አንዳንድ ጊዜ ምላሽ ለማግኘት ሁለት እና ሦስት ቀን ይወስዳል” ሲሉ አክለዋል።

    ተንታኞች እንዳሉት የስምምነቱ እንቅፋት በቴህራን ውስጥ ያለ የሥልጣን ሽኩቻ አይደለም። ነገር ግን ዋሽንግተን ለማቅረብ በተዘጋጀችው እና የኢራን አክራሪ ወገኖች ለመቀበል ፈቃደኛ በሆኑት መካከል ያለው ክፍተት ነው።

    ከአሜሪካ ጋር በሚደረገው የሰላም ድርድር የኢራን የዲፕሎማሲ ፊት የሆኑት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራጋቺ እና በቅርቡ የተቀላቀሏቸው የፓርላማው አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ ናቸው።

    ፖለቲካውን ከጀርባ ሆነው የሚዘውሩት ግን የአብዮታዊ ዘቡ አዛዥ አዛዥ አህመድ ቫሂዲ መሆናቸውን አንድ የፓኪስታን እና ሁለት የኢራን ምንጮች ለሮይተርስ አረጋግጠዋል።

    ቫሂዲ ቁልፍ ውሳኔ ሰጪ መሆናቸው በተኩስ አቁሙ ስምምነት ወቅትም ሆኑ ከዚያ በኋላ ከኢዝላማባድ ጋር ባለ ንግግር ወቅት ታይተዋል።

    ሮይተርስ በኢራን ስለተፈጠረው የአመራር ክፍተት ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩን ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አላገኘም። ከዚህ በፊት ግን በኢራን ውስጥ ባሉ አመራሮች መካከል መከፋፈል እንደሌለ እና የሥልጣን ሽኩቻ እንዳልተከሰተ በመግለጽ አስተየየት ሰጥቶ ነበር።

  14. ዶናልድ ትራምፕ ንጉሥ ቻርልስ ኢራን ኒውክሌር ጦር መሣሪያ ሊኖራት እንደማይገባ እንደሚያምኑ ተናገሩ

    ዶናልድ ትራምፕ ንጉሠ ቻርልስ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ሊኖራት አይገባም ብለው እንደሚያምኑ ተናገሩ።

    ዶናልድ ትራምፕ በዋይት ሐውስ ለንጉሡ በተዘጋጀ የእራት ግብዣ ላይ “ቻርለስ ከእኔ ጋር ይስማማል፤ ከእኔ በበለጠ ይስማማል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ትራምፕ በዚህ ንግግራቸው ላይ ቴህራንን "በወታደራዊ ኃይል አሸንፈናታል” ብለዋል።

    "ያ ተቃዋሚ [ቴህራን] በጭራሽ [እንዲኖረው] አንፈቅድም፤ ቻርልስ ከእኔ ጋር ይስማማል። ከእኔም በላይ፤ ያ ​​ተቃዋሚ የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዲኖረው በጭራሽ አንፈቅድም ።"

    የበርኪንግሃም ቤተ መንግሥት ቃል አቀባይ የትራምፕን ንግግር ተከትሎ ለቢቢሲ በሰጡት ምላሽ "ንጉሡ መንግሥታቸው የኒውክሌር መስፋፋትን ለመከላከል ያለውን የረዥም ጊዜ እና የታወቀ አቋም ያደግፋሉ" ብለዋል።

    ለአራት ቀናት የሥራ ጉብኝት አሜሪካ የሚገኙት ንጉሥ ቻርልሰ የአሜሪካን የነጻነት በዓል ከማክበር ባሻገር ከዩኬ ጋር የተፈጠረውን የግንኙነት መሻከር ይጠግናሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    ንጉሥ ቻርለስ ከባለቤታቸው ንግሥት ካሚላ ጋር በመሆን ሰኞ ዕለት ዋሺንግተን ሲደርሱ ደማቅ አቀባባል ተደርጎላቸዋል።

  15. በዓለም ላይ እጅግ ውድ የሆነውን ሃብት የሚቆጣጠረው ኦፔክ እና የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ሲለያዩ ምን ይፈጠራል?

    በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ምክንያት እየጨመረ የሚገኘው የነዳጅ ገበያ አዲስ ድንገተኛ ክስተት አስተናግዷል።

    የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ከፔትሮሊየም ላኪ አገራት ድርጅት (ኦፔክ) እንደምትወጣ አሳውቃለች።

    ኦፔክ እአአ በ1960 ነበር ባግዳድ ኢራቅ ውስጥ የተቋቋመው።

    በአምስት አገራት የተቋቋመው ኦፔክ የአባል አገራቱን ቁጥር 12 ማድረስ ችሎ ነበር።

    አሁን ግን የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ይህንን ቁጥርበአንድአጉድላዋለች።

    ተቋሙ ለዓመታት አባል አገራቱ የሚያመርቱትን ነዳጅ በመቆጣጠር የዓለም የነዳጅ ዋጋን ሲወስን ቆይቷል።

    የነዳጅ ዋጋ መጨመር ሲፈልግ ምርት ይቀንሳል፤ ዋጋው ለማረጋጋት ደግሞ አገራቱ ምርቱን እንዲጨምሩ ያደርጋል።

    የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ በተቋሙ ውስጥ አባል ብቻ ሳትሆን ቁልፍ ከሚባሉት ተርታ አንዷ ነበረች።

    የኦፔክ ምርት በሳዑዲ አረቢያ ቁጥጥር ስር ቢሆንም፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ሁለተኛው ከፍተኛ የመጠባበቂያ ምርት አቅም ነበራት።

    ይህም አገሪቱን አቅም ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነው።

    ሆኖም ግን ኦፔክ እያንዳንዱ አገር ምን ያህል ነዳጅ ማምረት እንደሚችል የሚያስቀምጠው ገደብ አለ።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ በቀን ከ3 እስከ 3.5 ሚሊዮን በርሜል ማምረት ተፈቅዶላታል።

    በቀን እስከ 5 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ የማምረት አቅም ላላት አገር አነስተኛ ቁጥር ነው።

    በቀላል አነጋገር የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ገንዘብ የማግኘት እድሏን በእጅጉ ቀንሶታል።

  16. በቴህራን እና ዋሺንግተን መካከል የሚካሄደው ንግግር መቋጫ ባለማግኘቱ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደው ጦርነት ዳግም ሊቀሰቀስ ይችላል በሚል ስጋር የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ አሻቀበ። ረቡዕ ዕለት ማለዳ የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል 111 ዶላር መሸጡ ተዘግቧል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተካሄደ የነበረው ውይይት በመቋረጡ የእስያ የነዳጅ ገበያ ዳግም ጭማሪ አሳይቷል።

    ሰኞ ዕለት የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በ3 በመቶ ጭማሪ በማሳየት በበርሜል 109 ዶላር መሸጡን ቢቢሲ ዘግቧል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን እና በአሜሪካ በመዘጋቱ የዓለም የነዳጅ አቅርቦት ተስተጓጉሏል።

    ኒውዮርክ ታይምስ እንዲሁ በአሜሪካ አማካይ የነዳጅ ዋጋ የኢራን ጦርነተ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በከፍተኛ ሁኔታ እያሻቀበ መሆኑን ዘግቧል።

    ማክሰኞ ዕለት በአሜሪካ የነዳጅ ዋጋ በአማካይ በ4.18 በጋሎን ጭማሪ ያሳየ ሲሆን ይህም የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ከተጀመረበት እአአ ከ2022 ወዲህ ከፍተኛው መሆኑን የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

  17. ትራምፕ፣ ቴህራን አሜሪካ በተቻለ ፍጥነት የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት ትፈልጋለች አሉ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ማክሰኞ ዕለት በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን “የመፈራረስ አደጋ የተጋረጠባት መሆኗን” እና የመሪዎቿን ሁኔታ እስክታውቅ ድረስ አሜሪካ የሆርሙዝ ወሽመጥን በፍጥነት እንድትከፍት መጠየቋን ተናገሩ።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ ከኢራን ጋር መልዕክቱን መቼ እንደተለዋወጡ ያልገለጹ ሲሆን ከቴህራን ወገንም የተሰማ ምላሽ የለም።

    “ኢራን ‘የመፈራረስ አደጋ የተጋረጠባት መሆኗን’ ነግራናለች። የመሪዎቻቸውን ሁኔታ እስኪለዩ ድረስ (ያንን ማድረግ ይችላሉ ብዬ አምናለሁ) በተቻለ ፍጥነት ‘የሆርሙዝ ውሽመጥን በተቻለ ፍጥነት እንድንከፍት’ ይፈልጋሉ” ብለዋል።

    ሮይተርስ ለዋይት ሐውስ በትራምፕ የማኅበራዊ ልጥፍ ዙሪያ ላቀረበው ጥያቄ ወዲያውኑ ምላሽ አላገኘም።

    ትራምፕ ኢራን ለሁለት ወራት የቆየውን ጦርነት ለመፍታት ባቀረበችው አዲስ የመደራደሪያ ሃሳብ ደስተኛ አለመሆናቸውን የአሜሪካ ባለሥልጣናት ለሮይተርስ የዜና ወኪል ተናግረው ነበር።

  18. የባሕረ ሰላጤው አገራት ለኢራን ጥቃቶች ስለሚሰጡት ምላሽ ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ሊወያዩ ነው

    የባሕረ ሰላጤው ትብብር ምክር ቤት አባል አገራት መሪዎች የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል ሳዑዲ አረቢያ ውስጥ ሊሰበሰቡ መሆኑን ሮይተርስ ዘገበ።

    የመሪዎቹ ስብሰባ የሚያተኩረው ሁለት ወር በሞላው ጦርነት ለዘነቡባቸው በሺህዎች የሚቆጠሩ የኢራን የሚሳዔል እና ድሮን ጥቃቶች ምላሽ ማዘጋጀት ላይ እንደሚሆን ዜና ወኪሉ ምንጮች ጠቅሶ ዘግቧል።

    በአሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት የተከፈተባት ኢራን በስድስቱም የባሕረ ሰላጤው ትብብር ምክር ቤት አባል አገራት የሚገኙ የኤነርጂ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    ከአሜሪካ ጋር ግንኙነት ያላቸው ተቋማት እና ሌሎች የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እንዲሁም ወታደራዊ ይዞታዎችንም አጥቅታለች።

    ሮይተርስ የጠቀሰው የሳዑዲ መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው የኳታር፣ ኩዌት እና ባህሬን መሪዎች እንዲሁም የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በስብሰባው ለመሳተፍ ጅዳ ገብተዋል።

    የምክር ቤቱ አባል የሆነችው ኦማን በማን እንደምትወከል እስካሁን አለመታወቁም ተጠቅሷል።

    የባሕረ ሰላጤው ምክር ቤት ለጦርነቱ በቂ ምላሽ አልሰጠም በሚል ከኤምሬቶች ትችት ቀርቦበት ነበር።

  19. ግዙፉ የነዳጅ ኩባንያ ቢፒ የኢራን ጦርነት ከጀመረ ወዲህ ትርፉ በእጥፍ ማደጉን ገለጸ

    ግዙፉ የነዳጅ ኩባንያ ቢፒ የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ የነዳጅ ዋጋ በመጨመሩ ትርፉ ከእጥፍ በላይ ማደጉን አስታወቀ።

    ቢፒ በነዳጅ ንግድ ውስጥ "እጅግ በጣም ጥሩ" አፈጻጸም ማሳየቱን ገልጾ ከጥር እስከ መጋቢት ባሉት ወራት ብቻ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ ማግኘቱን ይፋ አድርጓል።

    ይህ አሃዝ ተንታኞች ከጠበቁት በላይ መሆኑን የገለጸው ኩባንያው፣ ባለፈው ዓመት በተመሳሳይ ወቅት ካስመዘገበው 1.38 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ በእጥፍ እንደሚበልጥ ተናግሯል።

    ይህ ትርፍ የተመዘገበው አዲሷ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሜግ ኦኔል ኃላፊነታቸውን ከተረከቡ በኋላ ነው።

    የካቲት 21/2018 ዓ.ም. የተጀመረው የኢራን ጦርነት የነዳጅ ዋጋ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል።

    ጦርነቱን ተከትሎ 20 በመቶ የሚሆነውን የዓለም የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ አቅርቦት የሚያጓጓዝበት የሆርሙዝ ቁልፍ የባህር ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ ተዘግቷል።

    ብሬንት ድፍድፍ የነዳጅ ዘይት በአሁኑ ወቅት በበርሜል 110 ዶላር እየተሸጠ ሲሆን፣ የኢራን ጦርነት ከመጀመሩ በፊት ዋጋው 73 ዶላር አካባቢ ነበር።

    ኦኔል "ኢንዱስትሪውን በግጭት እና ተግዳሮት በሞላበት ወቅት" ኩባንያውን መቀላቀላቸውን ተናግረዋል።

    ቢፒ "ደንበኞች እና መንግሥታት በሚፈልጉበት ቦታ ነዳጅ እንዲያገኙ፣ በሰዎች ሕይወት ላይ ሊያስከትል የሚችለውን መስተጓጎል ለመቀነስ በመሥራት እየረዳ" እንደሆነ ተናግረዋል።

  20. የጀርመኑ ቻንስለር የኢራን አመራሮች አሜሪካን “እያሳፈሯት ነው” አሉ

    የጀርመኑ ቻንስለር ፍሬድሪክ መርዝ ሰኞ ዕለት ባደረጉት ንግግር የኢራን አመራሮች አሜሪካ ወደ ፓኪስታን አምርታ ያለ ውጤት እንድትመለስ በማድረግ “አሳፍረዋታል” ማለታቸውን ሮይተርስ ዘገበ።

    ቻንስለሩ ይህንን ያሉት በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ይደረጋል ተብሎ የነበረው የሁለተኛ ዙር የሰላም ውይይት ሳይካሄድ ከቀረ በኋላ ነው።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል መርዝ አሜሪካ ከኢራን ጦርነት ለመውጣት ያዘጋጀችው ስልት መኖሩ እንደማይታያቸው መናገራቸውን ጨምሮ ገልጿል።

    በአሜሪካ እና በአውሮፓውያኑ የሰሜን ጦር ቃል ኪዳን (ኔቶ) አባል አገራት መካከል በኢራን ጦርነት ዙሪያ ልዩነት አለ።

    ቻንስለሩ ሰኞ ዕለት በመርስበርግ ከተማ ለተማሪዎች ንግግር ባደረጉበት ወቅት አሜሪካኖች ወደ ኢዝላምባድ እንዲጓዙ እና ያለ ምንም ውጤት እንዲመለሱ በማድረግ ረገድ "ኢራናውያን በመደራደር በጣም የተካኑ ናቸው፤ ወይም ባለመደራደር ክህሎት ያላቸው ናቸው" ብለዋል።

    “በኢራን አመራር ሙሉ ሕዝቡ [አሜሪካውያን] ነው እንዲያፍር የተደረገው፤ በተለይ የአበዮታዊ ዘብ በሚባለው። እናም ተስፋ የማደርገው በተቻለ ፍጥነት [ጦርነቱ] እንዲጠናቀቅ ነው” ማለታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኔቶ አጋሮችን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት የባሕር ኃይላቸውን ባለመላካቸው ተችተዋል። የኢራን ጦርነት ከተጀመረ አንስቶ ወሽመጡ በመዘጋቱ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።