ቀጥታ, በቀጣይ ሳምንት ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ትራምፕ ተናገሩ

ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ለማራዘም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት በቀጣይ ሳምንት ስምምነት ላይ እንደሚደረስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኤቢሲ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናገሩ።

ጭምቅ ሃሳብ

ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ተመድ እስራኤል የሊባኖስን አምባ መቆጣጠሯን በተመለከተ አስቸኳይ ውይይት አካሄደ

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እስራኤል የሊባኖስን ጥንታዊ አምባ - ቢውፎርትን በቁጥጥር ሥር ማዋሏን በተመለከተ ትናንት አስቸኳይ ውይይት አካሄደ።

    በተመድ የሩሲያ አምባሳደር ቫስሊ ነቤንዝ “እስራኤል እና ሊባኖስ በአሜሪካ አሸማጋይነት የደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነት እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት እንድትፈጽም ከለላ ሰጥቷል” ብለዋል። ሊባኖስ የጋዛ ሰርጥ እጣ ፈንታ እንደሚጠብቃትም አክለዋል።

    በተመድ የፈረንሳይ ልዑክ ጀሮም ቦንፎን ውይይቱ እንዲካሄድ አገራቸው ጥሪ ማቅረቧን ጠቅሰው “እስራኤል ራሷን የመለካከል መብት ቢኖራትም ሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ምክንያታዊ አይደለም” ብለው ንግግር አድርገዋል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹኃን እንደተጎዱ እና እንደተፈናቀሉ የፈረንሳዩ ተወካይ ተናግረዋል።

    የአሜሪካ ተወካይ ማይክል ጄ ዋልዝ በበኩላቸው፤ድርድርን ጨምሮ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።

    “ሕጋዊው የሊባኖስ መንግሥት በቴህራን ከሚደገፈው አሸባሪ አገሪቱን ነጻ ለማውጣት ተነሳሽነት አሳይቷል” ብለዋል።

    የሊባኖስ ተዋካይ አሕመድ አራፋ ደግሞ መንግሥታቸው ነገሮችን ለመቆጣጠር ቢሞክርም “እስራኤል እንደ ሁልጊዜው ቀጣናዊውን ሁኔታ እየተጠቀመችበት ነው” ብለዋል።

    እስራኤል ሐኪሞችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ትምህርት ቤቶችን እና የፀጥታ ተቋማትን ዒላማ በማድረግ “ስልታዊ የውድመት ዘመቻ” መክፈቷንም ጠቅሰዋል።

    በተመድ የእስራኤል ልዑክ ዳኒ ዳኖን “አንድ ቀን ተነስተን ሊባኖስ ለመግባት አልወሰንም። አማራጭ አጥተን ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ኢራን ሄዝቦላህን በእጅ አዙር መጠቀም መቀጠሏን ጠቅሰው፤ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ቢደረስም “ሄዝቦላህ ሚሳዔል እና ድሮን መተኮስ” እንዳላቆመ ተናግረዋል።

  2. በቀጣይ ሳምንት ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ትራምፕ ተናገሩ

    ከኢራን ጋር የተኩስ አቁም ለማራዘም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት በቀጣይ ሳምንት ስምምነት ላይ እንደሚደረስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኤቢሲ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናገሩ።

    “አሁን ላይ ነገሮች በጣም ጥሩ ናቸው። ውስን ችግር ነበር፤ ነገር ግን እንዳያችሁት በፍጥነት ፈትቼዋለሁ” ሲሉ በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል።

    ትራምፕ ችግር ብለው የጠቀሱት እስራኤል በሊባኖስ ላይ የምታደርሰው ጥቃት ኢራንን ማስቆጣቱን ነው።

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታውቃለች። እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    ትራምፕ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    ትራምፕ “ሄዝቦላህን አትተኩሱ ብያቸዋለሁ። ቢቢ [ኔታንያሁ] እንዳይተኩስም ነግሬዋለሁ። ሁለቱም ተኩስ አቁመዋል” ሲሉም አክለዋል።

    በቀጣይ ሳምንት የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል ብለው እንደሚያምኑም ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።

  3. ሩሲያ በዩክሬን ከተሞች በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎች ተገደሉ

    ሩሲያ በዩክሬን ዋና ዋና ከተሞች ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ ዘጠኝ ሰዎች እንደተገደሉ እና ብዙዎች እንደቆሰሉ ተገለጸ።

    በዲፕሮ ከተማ አምስት ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ተጎድተዋል። ዛሬ ንጋት ላይ በደረሱ ጥቃቶች በመዲናዋ ኪቭ አራት ሰዎች መገደላቸው እና 51 መቁሰላቸውም ተዘግቧል፤ 35 ያህሉ ደግሞ ሆስፒታል ገብተዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ቪታሊ ክሊሽኮ እንዳሉት ሁለት ግዙፍ የመኖሪያ ሕንጻዎች የተመቱ ሲሆን፤ ሰዎች በፍርስራሽ ሥር ተቀብረው ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።

    ዩክሬን ባለፈው ወር የድሮን ድብደባ በመፈጸሟ በምላሹ “ስልታዊ ጥቃት” ለማድረስ ሞስኮ ስትዝት ቆይታለች።

    ሩሲያ በቁጥጥሯ ሥር ባዋለችው የዩክሬን ሉሀንስክ ግዛት በደረሰው የድሮን ጥቃት 21 ሰዎች ተገድለዋል።

    የኪቭ ከንቲባ ነዋሪዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል። “ጠላታችን በባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት እየፈጸመ ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

    በአብዛኞቹ የዩክሬን ከተሞች የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደወሎች እየተሰሙ ነው። በማዕከላዊ ኪቭ ጭስ መታየቱም ተገልጿል።

    በሌላ በኩል በሩሲያ ኢልስኪ የነዳጅ ማቀነባበሪያ የደረሰ ጥቃት እሳት ማስነሳቱ ተገልጿል።

    ኪቭ ውስጥ የበርካታ ድሮኖች እና ፍንዳታ ድምጽ እየተሰማ ይገኛል። ሞስኮ የፈጸመችው ጥቃት በነዳጅ ማደያ እሳት አቀጣጥሏል።

  4. ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረሱን ለማቆም መስማማቱን ሊባኖስ ገለጸች

    ሄዝቦላህ በእስራኤል ላይ ጥቃት ማድረስ እንዲያቆም ከአሜሪካ የቀረበለትን ሐሳብ መቀበሉን ሊባኖስ አስታወቀች።

    እስራኤልም በሊባኖስ መዲና ቤሩት ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷም ተገልጿል።

    አሜሪካ የሚገኘው የሊባኖስ ኤምባሲ “አሜሪካ ሁለቱም ወገኖች ጥቃት እንዳያደርሱ ያቀረበችውን ምክረ ሐሳብ ሄዝቦላህ ተቀብሏል” ብሏል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁም ስምምነት ላይ መደረሱን አረጋግጠዋል።

    ሆኖም “ሄዝቦላህ ከተሞቻችን እና ዜጎቻችን ላይ ጥቃት ከፈጸመ ግን ቤሩትን እንደበድባለን” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኔታንያሁ እና ከሄዝቦላህ ተወካዮች ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰው “ተኩስ ለማቆም ተስማምተዋል” ብለዋል።

    እስራኤል በሊባኖስ የምታደርሰው ጥቃት የኢራን እና አሜሪካን የተኩስ አቁም ስጋት ውስጥ እንደሚጥል ቴህራን መግለጿ ይታወሳል።

    የሊባኖስ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ “ሄዝቦላህ እስራኤል ላይ ጥቃት ካልፈጸመ እስራኤልም በቤሩት ጥቃት እንደማታደርስ ተስማምተናል” ብሏል።

    የተኩስ አቁሙ በሒደት “ሌሎች የሊባኖስ አካባቢዎችን እንደሚሸፍን” ተገልጿል።

    ኔታንያሁ በበኩላቸው “የእስራኤል መከላከያ ኃይል በታቀደው መሠረት በደቡብ ሊባኖስ ዘመቻውን ይቀጥላል” ብለዋል።

    ሁለቱ ወገኖች ተኩስ ለማቆም መስማማታቸውን ትራምፕ ከገለጹ በኋላ የተወሰኑ ግጭቶች መነሳታቸው ተዘግቧል።

  5. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሦት ወራት በፊት የተጀመረውን የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ለመቋጨት የሚያስችለውን ስምምነት ለማስተካከል ፍላጎት እንዳላቸው የዋሽንግተን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ለውጦቹ በሆርሙዝ ወሽመጥ እና የተብላላ የዩራኒየም አወጋገድ ጋር የተያያዙ እንደሆኑ በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል።

    ዋይት ሐውስ አስተያየት እንዲሰጥ ቢጠየቅም ምላሽ አልሰጠም።

    የኢራን ዋና ተደራዳሪ መሐመድ ባገር ጋሊባፍ እሑድ ዕለት የኢራን መብት ሙሉ ለሙሉ እስካልተጠበቀ ድረስ ቴህራን ምንም ዓይነት ስምምነት አትፈጽምም ብለዋል።

    የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለማራዘም በሚያስችለው ማዕቀፍ ላይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር አርብ ዕለት ለንግግር ቢቀመጡም፤ ስብሰባው ቀጣይ እርምጃዎች ላይ ግልፅነት ሳይኖረው ተጠናቋል። ሙሉውን እዚህ ያንብቡ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ እና የኢራን ስምምነትን ለማረም ፍላጎት እንዳላቸው ተነገረ