አሜሪካ ከወታደራዊው ዘመቻ “አቻ” በሆነ ደረጃ በኢራን ፋይናንስ ላይ ጫና ማሳደር የሚያስችል እቅድ እያጠናቀቀች መሆኗን የግምጃ ቤት ኃላፊው ስኮት ቤሴንት ተናገሩ።
የትራምፕ አስተዳደር የኢራን ኢኮኖሚን ይበልጥ
ለማሽመድመድ ያቀደበትን እቅድ ተግባራዊ የሚያደርገው አሜሪካ እና ኢራን በቶሎ ስምምነት ላይ ካልደረሱ መሆኑን የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ
ፕሬስ ዘግቧል።
የግምጃ ቤት ኃላፊው ቤሴንት ትናንት በሰጡት
መግለጫ፤ የኢራን ፋይናንስ ላይ ጫና የሚያሳድረው “ኦፕሬሽን ኢኮኖሚክ ፊውሪ” እየተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል።
ፕሬዝዳንት ዶናልድ
ትራምፕ ኢራን ላይ ወታደራዊ ጥቃት ሲከፍቱ ለዘመቻው የተሰጠው ስያሜ “ኦፕሬሽን ኢፒክ ፊውሪ” የሚል ነበር። ከወታደራዊው ዘመቻ ጋር ተመሳሳይ መጠሪያ የሚይዘው
ኢኮኖሚያዊ ጫና የቦንብ ድብደባው እኩያ እንደሚሆን ቤሴንት ገልጸዋል።
ኢራን ሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራትን
በመደብደብ ስህተት ሰርታለች ያሉት የግምጃ ቤት ኃላፊው፤ በአሁኑ ሰዓት ጥቃት የተፈጸመባቸው በባንክ ስርዓቶቻቸው ውስጥ ያሉትን የኢራን ፈንዶች “ግልጽ” ያደረጉ መምጣታቸውን ጠቅሰዋል።
እነዚህ አገራት በባንክ ስርዓታቸው ውስጥ የሚገኙ
የኢራን አብዮታዊ ዘብ አመራሮች አካውንቶችን እንቅስቃሴ እንዲያግዱ አሜሪካ መጠየቋንም አስታውቀዋል።
በተጨማሪም አገራቱ የኢራንን ነዳጅ እንዳይገዙ
ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል ብለዋል። አገራቱ በባንክ ስርዓቶቻቸው ውስጥ የኢራን ገንዘብን የሚያስቀምጡ ከሆነ ሁለተኛ ደረጃ ማዕቀብ
እንደሚጣልባቸው ገልጸዋል።
የኤፒ ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ ሁለተኛ ደረጃ
ማዕቀብ የሚጣለው ከኢራን ጋር የንግድ ልውውጥ በሚያደርጉ፣ ግለሰቦች፣ ተቋማት እንዲሁም በኢራን ቁጥጥር ስር ባሉ መርከቦች ላይ
ነው። አሜሪካ አጋር እንደሆነችው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እንዲሁም እንደ የዋሽንግተን ተቀናቃኟ ቻይና ያሉ አገራትም ማዕቀቡ
ሊደርስባቸው ይችላል።
ቤሴንት፤ “የኢራንን ነዳጅ የምትገዙ ከሆነ፣
በባንኮቻችሁ ውስጥ የኢራን ገንዘብ ተቀምጦ ከሆነ ሁለተኛ ደረጃ ማዕቀብ ልንጥልባችሁ ፈቃደኛ ነን ብለን ለኩባንያዎች፣ ለአገራት
ነግረናቸዋል” ብለዋል።
ይህ እርምጃ ኢራን ውስጥ “የተመለከትነው [ወታደራዊ]
እንቅስቃሴ የፋይናንስ እኩያ እንደሚሆን ኢራናውያን ማወቅ አለባቸው” ሲሉም አስጠንቅቀዋል።
ከመግለጫው በኋላ የአሜሪካ ግምጃ ቤት ከኢራን ጋር ግንኙነት አላቸው ባላቸው ግለሰቦች፣ ድርጅቶች እና መርከቦች ላይ ማዕቀቦቹን መጣሉን ይፋ አድርጓል። ማዕቀብ የተጣለባቸው ሦስት ግለሰቦች፣ ዘጠኝ መርከቦች እና 17 ተቋማት ናቸው።